ዮሐንስ ሞላ's Blog, page 15

August 13, 2016

አለማወቅህን ለመጋረድ…

ስትቀልድበት አብሮ መሳቁ የልብ ልብ ሰጥቶህ ከሆነ እዚህ ያደረሰህ ተሳስተሃል። የሚጎዳውን እና የሚጠቅመውን መርምሮና ለይቶ ተገቢውን ምላሽ ይሰጣል እንጂ፥ የጉራጌ ማኅበረሰብ በንቃት (consciously) ኗሪ ነው። ለዚያም ነው ሥራን ካለመናቅና በኅብረት ከመንቀሳቀስ አንስቶ፣ ሰብአዊ መብቱን ተጠቅሞ፥ ገና ድሮ በየክፍለ አገራቱ ተንቀሳቅሶ እስከመኖር የደረሰው።


 


አርአያ የሚሆን የቁጠባ ባህሉም፣ በነጻነትና በስርዓት የመኖሩ ውጤት ነው። የዚያኑም ያህል ደግሞ፥ በየደረሰበት በፍቅርና በሰላም ተቻችሎ በመኖሩ ይወሳል እንጂ በክፉ አይነሳም። ባለማወቅ ቢያንጓጥጡበትና የሕይወት መመሪያውን ባለመገንዘብ ቢቀልዱበት፣ አብሮ እየሳቀ ዝም ብሏቸው ኖሮ፥ ውሎ አድሮ በክፉ በደግ ማንነቱን በሥራው ነው የሚያሳየው።



ግፍና ጭቆናን ማንም አይወድም። የበደልን ቀንበርም ማንም እስከዘላለሙ ችሎ አይሸከምም። የጉራጌ ማኅበረሰብም ሥራ የመውደዱን እና ሰላም የመሻቱን ያህል አምባጓሮ ውስጥ ራሱን ለማግኘት አይፈልግም እንጂ፥ “በሰላምና በሽምግልና ማኅበራዊ ችግሮቻችንን እንፍታ” ሲል እምቢ ብለውት ሲረግጡት ይረግጣል። ረግጬህ ልግዛህ ሲባል አሻፈረኝ ይላል። ሕግና ስርዓትን ዘርግቶም ባህሉን አክብሮ ኗሪ ነው።


 


በማኅበረ ፖለቲካው በጉራጌዎች የተደረጉ እምቢባይነቶች ሞልተዋል (እንዲህ እንደዛሬው ሰው በጎጥ ተከፋፍሎ ‘የአማራ’ ‘የጉራጌ’ መባባል ሥር ሳይሰድ በፊት፥ በ’ኢትዮጵያዊነት’ ስምና ስሜት። በአገራዊ አጀንዳ ‘የጉራጌ ተቃውሞ’ የሚባል ኖሮ አያውቅም። ያው ሀሳቡም መጤ ነው)። ከኢትዮጵያዊነት ጉዳዮች ባሻገር ከድል በኋላ ወደ ሥራ ስለሚሄድ፣ ታሪክም በባለጊዜዎች ስለሚመዘገቡ እንጂ ብዙ ታሪኮች አሉ። የተጻፈውም ቢሆን በበቂ ሁኔታ መስካሪ ነው። ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴስ ጨቦና ጉራጌ አውራጃ አይደል ተወልደው ያደጉት! በየዘርፉ ዞር ዞር ብለህ ታዘብ፥ የሕይወት ታጋዮች ሞልተውልሃል፡


 


ከቤትህ ዙሪያ ልስማ ካልክ የአባቴ አባት በጣልያን ተሰቃይቶ መገደሉን እናቴ ትተርክልሃለች። ተተኩሶበት ሳይሆን፣ ተይዞ፣ ዐይኑ ተጎልጉሎ እና ሌላ ሌላም ስቃይ ደርሶበት መሞቱን የነበረ ያህል ታወራልሃለች። (አባቴ “ያኔ 12 ዓመት ብሆን ነው” ይላል።)


 


ልብ አድርግ! ስለአባቴ አባት ነው፥ እናቴ እሷ ሳትወለድ ስለሞተው አያቴ የተነገረውን ታሪክ የምትተርክልህ። እንጂማ አባቷም ቀላል አልነበሩም። ደርሼባቸው ከአንደበታቸውም ሰምቻለሁ።


 


“መድፍና መትረየስ ጥይት ሲጓረሱ


አሳላፊ ነበር የማሩ ገረሱ” ስለተባለለት ደጃዝማች ገረሱ ዱኪ፣ አባ ቦራ (አያቴ አገልጋዩ ሆነው አሳልፈዋል) እና ስለጀግኖች አርበኞች ተጋድሎ፥ የታሪክ መጽሐፍ ማንበብ ሳልጀምር በፊት ከእርሳቸው ነበር የምሰማው።


 


በቅርቡ ታሪኳ በሰፊው የተነገረላት ሴታዊት (feminist)፣ የቃቄ ውርድወትን ተመልከትና ያልተዘመረላቸውን ሌሎች ብዙዎችን አስብ። ‘አይ ዘመኑ ወዲህ ይቅረብልኝ’ ካልክ፥ የተደላደለ ኑሮውን ትቶ በረሀ የገባው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋም አለልህ። (እንግዲህ ጉራጌ ጥርስ ከነከሰብህ፣ “ከፈለግክ ዱላም እንማዘዝ” ካለህ፥ ምን ክፉ ብትሆን እንደሆነ ራስህን መፈተሽ ነው።) “ቆይ እስኪ እንየው” ብሎ ተስፋ ባለመቁረጥ በሰላም የሚማጸን ከፈለግክ ደግሞ፥ ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም ይጠቀሱልሃል። (እንግዲህ ልብ አድርግ፣ ጫፍ ጫፉን ነው የማወራልህ። መሀል መሀሉን ገምተው።)


 


ወዳጄ፥ አለማወቅህንማ በከንቱ ዘለፋ አትጋርደው!


 


Stop your racist remarks against the Gurage people!, or die now with it!


 


#Ethiopia #StopKillingCivilians

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on August 13, 2016 05:12

August 12, 2016

የሀይማኖት ነጻነት ይከበር!

ህግ እንዳከበረ ሰው ለመመጻደቅ አይደለም መቼም። ግን ሌሎች ትዕዛዛቱን ሲጥስ ስለኖረ፣ ከምዕመኑ እኩል “ንስሀ ግባ” ብሎ መወትወት ቢቀር፣ በዘርና በሀይማኖት ለያይቶ ሊደላደል እየዳከረ፣ በጠራራ ፀሐይ ሕዝብን እንደጤፍ ሲቆላና እንደምንም ሲያራግፍ፣ ክቡር ሰውነትን ባለቤት እንደሌለው ሲያንገላታ ባላየ ባልሰማ ኖረው (ለእግዚዮታ እንኳን ጥሪ ማድረግ አንድ ነገር ነበር)….


 


“ለቀደሙት አትግደል እንደተባለ ሰምታችኋል፤ የገደለም ሁሉ ፍርድ ይገባዋል እኔ ግን እላችኋለሁ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፡፡” ማቴ. 5፡ 21-22 የሚለውን ትዕዛዝ ጠቅሰው ያላወገዙትና ጠብመንጃውን እንዲዘቀዝቅ ስለነፍስ ያልወተወቱት አካል፣ ሲጨንቀው “ኑ አማልዱኝ… ሕዝብን ዐይኑን ያዙልኝና ማሞኘቴን ካቆምኩበት ልቀጥል።” ሲል…


 


“ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።” ~ 1.ቆሮ.6: 19-20


 


“በዋጋ ተገዝታችኋልና የሰዎች ባርያ አትሁኑ” ~ 1ቆሮ.7፡23


 


“እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” ~ ቆላ.1፤13-14


 


“ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” ~ ገላ.4:7


 


እና ሌላም ተብሎ የተነገረውን፣ ‘በክርስቶስ ክርስቲያን ተብለሀልና ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ’ እያሉ ሲሰብኩት የኖሩትን ሕዝብ፣ ለመሸምገል ማሰቡ እንደምን ቀለላቸው?


 


ለነገሩ፣ ጥላሁን ገሰሰ ሞቶ ያኔ የነበሩት ጳጳስ ለቅሶ ቤት ሊያጽናኑ ሄዱ ተብሎ ወሬ ሲነገር፣ ጥሌን ብንወደውም፣ ስለዘላለማዊ ሕይወት ለመስበክ ሜዳና ፈረሱ ገጠሙላቸው ብለን ኢቲቪው ላይ ቸክለን ስንሰማ “ጥላሁን አልሞተም። ቤተክርስቲያናችን ሞተ የምትለው ምንም ሳይሰራ ያለፈን ሰው ነው…” ምናምን ብለው ያሸማቀቁንንም አንረሳውም።


 


እንደአቡነ ጴጥሮስ ‘ጽአ እርኩስ መንፈስ!… ሕዝቤን ልቅቅ’ ብሎ ጋንጩራቱን ጭራ የሚያስበቅል አባት እንናፍቃለን። ምህረቱ ለዘላለም ይሁን!!


 


የሀይማኖት ነፃነት ይከበር!


 


!


 


#Ethiopia #StopKillingCivilians

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on August 12, 2016 05:15

August 11, 2016

ሀገሬን ከነኗሪዎቿ…

13925175_1450435844972892_1002811786806231956_nበስፖርቱም ሆነ በሌላው ጉዳይ አገሬን ከነኗሪዎቿ እንደ ሮቤል ኪሮስ ያስተዋወቀልኝ የለም። እንደሱ፥ በደልና ግፉን ሁሉ ባንድ ላይ ሸክፎ ለዓለም ያሳየልኝ የለም። ሙስናውን፣ ውጥንቅጡን፣ የወጣቱን ጉስቁልናና መገፋት፣ የስራ ማጣቱን፣ ሞያ ማቃለሉን፣ የሆድ ስፋቱን፣ የፖለቲካና የዘር መድልዎውን፣ የኑሮ ልዩነቱን (‘ሰላም ውሎ መግባት’ን ካለማወቅና ‘የጠሉትን የመቃወምን ዋጋ’ ካለመተመን፣ እስከ ‘የፈለጉትን ልዩ ነገር መሞከር’ መቻል ድረስ)… “መተዋወቅ” ላይ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የሆነ መጭበርበር ደርሶባታል። ሀቀኛ ኗሪዎቿም ተበድለዋል።


 


ከትናንት በስቲያ ግን በሮቤል ቀፈት በኩል ሁሉም ነገር ታየ። በእርሱ ከአቅም በታች በሆነ ችሎታ ኦሎምፒክ ላይ መሳተፍ ሁሉም ነገር ፍጥጥ ብሎ ተነገረ። ሮቤልም አባቱም ያውቃሉ ብዙ ችሎታ እያላቸው ቤት የቀሩ ድንቅ ዋናተኞች እንዳሉ… ሌላ ሰው ተወክሎ ቢወዳደር የማሸነፍ እድል እንደነበረን… የሰውነት አቋሙን ዝርክርክነት (ፎቶው ላይ ወላ ተሰብስቦ ነው)… በምን መስፈርት እንደተመለመለና ባንዲራ ተሸካሚ እንደሆነ… እንዲህ ያሉ ትልልቅ ጉዳዮች ላይ አገርን ለመወከል ቀርቶ ለተራ የቀበሌ ሥራ፣ ሚኒማውን ማሟላት ማለት ዝምድና ወይም የፖለቲካ ትስስር መፍጠር ማለት እንደሆነ… ሌሎችም ብዙ ባለጊዜያት ያውቃሉ። ግን በቃ ሮቤል መሞከር የሚፈልገውን ነገር እንዲሞክርና “ለየት” ማለት እንዲችል፥ የአገሪቷን መስፈርት ያሟላል። እንደአባትና ልጅ ሊያሳፍር የሚገባ ጉዳይ ሳይቀር፥ እንደባለጊዜ ሲታይ አእምሮን ይደፍንና ያኮራል።


 


ከነኅሊና ከሆኑ ምን እውቀትና ጉጉት ቢሰንቁ፣ ሰተት አድርጎ የማያስገባውን የሥራና የሞያ ዓለም አሳየልኝ። በየትኛውም ዘርፍ፣ ሰው ምን ያህል ያሸበረቀ ሲቪ ቢኖረው፥ በልኩ የተሰራ ስራ ላይ ተወዳድሮ አገሩን ማገልገል ቀላል እንደማይሆንለት… በአንጻሩ፥ የሚፈለገውን ሞያዊ አቋም ያላሟላ ቦርጫም፥ ላዩ ላይ ተጣብቆ በሚያስጨንቀውም ሆነ፣ ሰፍቶት በሚወላለቅበት፥ የስራ ዓለም ላይ ገብቶ አገሩ ላይ መገልገልና ሕዝቧን መበደል መቻሉን አሳየልኝ። የራበውና ቤተሰብ ማስተዳደር ያለበት ሰው ህሊናውን ሸጦ፣ የማያምንበትን ሀሳብ እያራመደ ዳቦ ይገዛ ዘንድ የሚያስገድደውን የተጨማለቀ ሲስተም ፍንትው አደረገልኝ።


 


የተማሩና አገር ውስጥ መስራት ያልቻሉ ብዙ ሰዎች ለስደት ወጥተው በየበረሀው ቀርተዋል። የቀናቸውም በየሰው አገሩ ተበትነዋል። እንኳን የማይችሉትን ልዩ ነገር ለመሞከር ቀርቶ፣ የሚችሉትን ልዩ ነገር መስራት እንዳይችሉ በሀሳብ ልዩነታቸውና በፖለቲካ ተሳትፎአቸው የተነሳ ከየእስር ቤቱ ፍርግርግ ጀርባ የተወረወሩም ሞልተዋል። መንግስትን የሚቃወም መፈክር ያዛችሁ ተብለው ከዩኒቨርስቲ ትምህርት ገበታቸው ሳይቀር ተፈናቅለው ጥቃት የተፈጸመባቸውም አሉ። በየጎዳናው ለሰላማዊ ሰልፍ ወጥተው በግፍ ደማቸው የሚንዠቀዠቅ ወጣቶችም አይቆጠሩም። በአንጻሩ ደግሞ፥ የፖለቲካ ታማኝነትንና ዝምድናን ተገን አድርገው፥ ሳያንኳኩ፣ በተኙበት በሮች ተከፍተውላቸው ከቤት የሚጠሩ ቦርጫሞች አሉ። ይኼን ይኼን ሁሉ ሮቤል አሳየልኝ።


 


በአትሌቲክሱ እንኳን ብንመለከት፥ ብዙ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ለሌላ አገር ባንዲራ እየሮጡ ነው። ከአገር ቤት የሚገፉት፥ እንዲህ እንደሮቤልና አባቱ ያሉ የኅሊና ቦርጫሞች እየተመረጡባቸው ነው። ይህኔ፥ እሱ ቀፈቱን ለዓለም ባሳየበት ቅጽበት ቅስማቸው ተሰብሮ የስደት በርን ያማተሩ ብዙ ዋናተኞች ይኖራሉ። በሌላውም ዘርፍ እንዲሁ። ….እንጦጦ ሄደሽ ብትወድቂ ብትነሺ፣ አገር እቅፉን በሚደንቅ ብቃት ብትሮጪ፥ አትሌቲክስ ማኅበሩ ዙሪያ ዘመድ ከሌለሽ ማንም አያይሽም። ብለሽ ብለሽ ሲመርሽ፥ እዚያ ለሚሮጡት ጀላቲና ቀዝቃዛ ውሀ በመሸጥ ራስሽን ለማስተዳደር ትሞክሪ ይሆናል። …ይኼን ይኼን ሁሉ ብዙ ሳያወራ አሳየልኝ።


 


ሮቤል አገራችንን በዋና ለመወከል ወጥቶ፥ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ወክሎን ለዓለም አሳይቶልናል፣ እዚሁ እያለንም ለተጋረደብን ሰዎች ነገሮችን ገላልጦልናልና፥ ከእርሱ ይልቅ ፈልቅቆ ባሳየን አገር ላይ ዐይናችንን እንጣል።


 


የእርሱ ቦርጩን ማዝረክረክ የማሳፈሩን ያህል፣ የብዙ ቀልዶች መፈጠር ምክንያት ቢሆንም፥ እሱ እሱ እንዳያዘናጋንና መብታችንን ከመጠየቅ (ቢያንስ መበደላችንን በቅጡ ከመገንዘብ) እንዳያዘናጋን።


 


#Ethiopia #StopKillingCivilians

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on August 11, 2016 12:31

August 8, 2016

“…”

የሕዝብ ጩኸት ቢገፋ፣

የንጹህ ሰው ደም ቢደፋ

‘ምድር’ ሲባል ርቆ መጥቆ


ሰማያቱን ሰነጣጥቆ፥


ይጮኻል በልዩ ግርማ፣


ይሰማል በእዮር፣ ራማ፤

የሰው ስጋ ተፈትቶ፣


አይቀርም በብላሽ ከቶ፣


የኀዘን መቀነትን ፈትቶ፣


ዋይታ ነዝቶ፣ ዕንባ አራጭቶ፤


 


ከበደል ጋር ተመዝኖ፣


የክብሩን አክሊል ጭኖ፣


ከሰማይ ምኩራብ ዳምኖ፣


ዶፍ ይዘንባል


ለገፊዎች መአት ሆኖ፣


ለተገፊ ምህረት ገንኖ፤


 


ንጹሕ ቢወድቅ ሺ ይነሳል፣


ሺ ያቆማል፣ ሺ ይጠራል፤


ንጹሕ ቢጮህ ሺ ያነቃል፣


ሺ ይጣራል፣ ሺ ይሰማል፤


ንጹሕ ደምቶ ሺው ፀአዳ፣


ተሸላልሞ በፍቅር ዕዳ፤


 


የንጹሕ ደም ከእንባ ገጥሞ፥


ሰማየ ሰማያት ከርሞ፣


ወደ ምድር ሲከነበል፣


ሺ ይጠርጋል፣


ሺ ያጸዳል፤


ሺ ያቀናል፣


ሺ ያሰምጣል…


 


ወዮ ላንተ ለገዳዩ…


ግዳይ ጥለህ ስትጨፍር፥


ለሚረግጥህ ተከታዩ፣


ያፈራኸው በክፋትህ፣


ያቀናኸው በግፋትህ!


 


የበደል ጽዋህ ሲሞላ፣


ትንሳኤው ሲበሰር የሰው


በሀሴት ፋሲካው ሲበላ፣


አንተ ትኖራለህ ወድቀህ፣


ተዘርረህ በሞት ጥላ።  


 


/ዮሐንስ ሞላ/



 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on August 08, 2016 19:55

August 7, 2016

አምናለሁ… ይነጋል!

የሰው ደም ማየት አልችልም! መፈጠሬን ያስጠላኛል! ነስር ባቅሙ ቀኔን ይቀማኛል። ከስፖርት እንኳን ቦክስ አልወድም። ሁለት የማይተዋወቁ ሰዎች፣ ለመብት ትግል አይደለ፣ ለዳቦ አይደለ፣ ለጨዋታ ብለው እንኳን እንዲሁ ተያይዘው ሲተናነቁ ሳይ አልችልም። አቅመ ቢስ ነኝ! ደም ሳይ ያዞረኛል! (ይገርመኛል! እንዲህ ሆኖ እንኳን ትክክለኛው የወታደርነት ዲሲፕሊን ይማርከኛል። ‘ሳድግ ወታደር እሆናለሁ’ እል ነበር። እንደልጅ ምኞቴ ያላደረገብኝ አምላክ ይመስገን!)


 


ይኸው ብሎ ብሎ ስለሞት አሳሰበኝ። ሰው ከሥራ፣ ከተሳትፎዎች፣ ከስልጣን እና ከሌሎች ጉዳዮች ላይ ራሱን በገዛ ፈቃዱ እንደሚያሰናብት ሁሉ፥ በአግባቡ መኖር እና ማኖር ያልቻለ ሰው፥ ራሱን ከኑሮ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የሚያሰናብትበትን ስነልቡና አሰላሰልኩት። ስለዘላለማዊ ሕይወት ተብሎ መስበክ ይቅር ይባል ይሆናል እንጂ፥ ብዙ ራሳቸውን ማጥፋት የሚገባቸው ሰዎች ንጹሐንን በግፍና በገፍ እያጠፉ ነው። ራስን ከሥራ ብቻ ሳይሆን፥ ከኑሮም ላይ ማግለል እና “በቃኝ” ማለት እንደሽንፈትና ራስ ወዳድነት ብቻ መቆጠር የሚገባው አይደለም። አንዳንዴ ከንቱነትን እና የራስን ጭካኔ ማሸነፍም ነው። ለራስ ክፋት እጅ መስጠት ነው።


 


ሰው እንዴት የሰው ደም ለማፍሰስ ከእንቅልፉ ይነሳል??? ሰው እንዴት የእለት እቅዱ ውስጥ “መግደልና መደብደብ” ይኖሩታል??? ሰው ሲያሰቃዩ ውለውስ እንዴት ያንቀላፋሉ?? ከዚህ ሞት አይሻልም?! ሺህ ዓመት አይኖር! ሀብት ንብረትም ያልፋሉ! የራስ ዛሬ ባይስተዋል፥ የአምባገነን ጎረቤት ትናንት እንዴት ይዘነጋል?? ድምጾችስ በታፈኑት ልክ እንደሚፈነዱስ እንዴት ሳያውቁ ቀሩ??


 


እናም እመኛለሁ…


 


ምንም እንኳን፥ ፍትህ ሳይፈጸምበት ወንጀለኛ እንደዋዛ እንዲሞት ባልደግፍም (አሁን የአቶ መለስ የተቀላጠፈ ሞት እንዴት እንደሚያንገበግበኝ! ነገር ዓለሙን ቆጣጥሮት፣ ሸሩን ተብትቦ ከነወንጀሉ፣ ፍትህ ሳይፈጸምበት ሄደ። ነፍስ ይማር!) ብዙ ባለስልጣናት የንጹሀንን ደም ማፍሰስ ካላቆሙ፣ እስርና ግድያውን አቁመው ለመነጋገር ካልቀረቡ፥ ራሳቸውን ከኑሮ ላይ እንዲያገልሉ እመኛለሁ። ከቤተመንግስት እና ዙሪያዋ ብዙ የራስ ማጥፋት (suicide) ወሬዎችን ብሰማ እመኛለሁ።


 


ወታደሩስ፥ ይሄ ሁሉ ሰው አደባባይ ወጥቶ ተቃውሞውን ሲያሰማና ጥያቄዎችን ሲያነሳ፥ እንዴት እንደ አንድ ኗሪ “ምንድን ነው?” ብሎ ላይጠይቅ ቻለ? ስለተባለ ብቻ እንዴት ይተኩሳል? የመንግስት ወዳጆችና ካድሬዎች ቢሆኑስ፥ የፈለገውን ያህል በሆድ ቢተበተቡ፣ ይህንን ሁሉ ግፍ እያዩ እንዴት ተቃውሞ አያሰሙም? ተቃውሞ ማሰማቱ ቢቀር፥ እንዴት አፋቸውን ሞልተው ለመንግስት ይከራከራሉ? አንድ ሰው የስንት አውቶብስ ዋጋ አለው? ቁስንስ የሚፈበርከው ሰላም ያገኘ የሰው ልጅ አእምሮ አይደለም? አንድ ሰላም ባስ ቢቃጠል ነጠላ አሸርጣችሁ “እዬዬ” ስትሉ የነበራችሁ፥ በሁለት ቀናት ከመቶ በላይ ሰው ሲገደል ምን ተሰማችሁ??


 


መቼስ ዝም ብለው ደም እያፈሰሱ፣ እያሰሩ እና እየገረፉ በሰላም መኖር አይቻልም። የንጹህ ሰው ደም ሰማየ ሰማያትን ሰንጥቆ ያስተጋባል! እስካንገት ደርሶም ያንቃል! በምድረ በዳ መቅበዝበዝም ገንዘባቸው ይሆናል! የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ፥ መልካምም ሆነ ክፉ ሥራ ዋጋውን ያገኛል!


 


አምናለሁ…. ይነጋል!!!


 


#Ethiopia #StopKillingCivilians #OromoProtests #AmharaProtests

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on August 07, 2016 05:21

July 26, 2016

‘የአስተማሪ ምግብ…’

ዩኒቨርስቲ አስተምር የነበረ ጊዜ…


 


ከእለታት ባንዱ ቀን ቡና ልጠጣ ወጥቼ ጠረጴዛ የተጋራኋቸው ሁለት ባልደረቦቼ ብስጭትጭት ብለው ሲያወሩ ሰማኋቸው።


 


“ምንድን ነው እሱ?” አልኩኝ ከመቀመጤ።


 


“እንዴት እንዴት እንደጠገቡ እኮ…” አለኝ አንዱ።


 


(በኋላ ግራ ቀኙን ስቃርም የገባኝ ሁሉም በየጠረጴዛው ያወራ የነበረው ይህንኑ ጉዳይ ነበር።)


 


“እነማን ናቸው ደግሞ?”


 


“ሌላ ማን ይሆናል? እነዚህ የተረገሙ ናቸዋ”ብሎ ተማሪዎች ወደሚራመዱበት አቅጣጫ አገጩን ቆለመመው።


 


“ተማሪዎቹ? …ምን ተባለ ደግሞ?” አልኩት እንዲህ መነጋገሪያ የሆነውን ጉዳይ ለመስማት አቆብቁቤ።


 


“እዚህ ላውንጅማ ድርሽ አይሏትም። እንደውም በዲሲፕሊን ኮሚቴ መከሰስ አለባቸው።” አለኝ።


 


“ጋይስ እኛም እኮ መምህራን ነን። እንስማውና አብረን እንቃጠል።” አልኩ።


 


“ምን ባክህ፥ ሁለት ሴቶች ከውስጥ እየወጡ፣ አንዲት ጓደኛቸውን… ‘ተመለሽ ተመለሽ፥ ምግብ አልቋል’ አሏት። ‘ምንም’ ስትል፥ ‘አይ ያለው ለአስተማሪ የሚሆን ብቻ ነው’ አሏት። እንዲሰማ ጮክ ብላ…” አለኝ።


 


አተራረካቸውና አበሰጫጨታቸው ዘና አድርጎኝ ስለነበር፥ “እንግዲህ ተማሪዎች ላውንጅ ሄዶ በልቶ፣ የተማሪን ምግብ የመግዛት አቅም አለን ማለት ነው። በፊት እንኳን፥ አንዱ ጋ ለትምህርት ሲኬድ የፈረደባት ካሪና ተገዝታ “እኔም ተምሬ መጣሁ” አስብላ ታስሸልል ነበር።” ብዬ እንደመሳቅ አልኩ። አልሳቁልኝም። ተናደዋል።


 


እንግዲህ “ለአስተማሪ የሚሆን ለተማሪ የማይሆን” (that teachers can’t afford, but students) የምግብ ዓይነት መኖሩ ነበር እንዲያ ያተከናቸው።


 


ቀን ተቆጥሮ ተማሪዎቹም ተከሰሱ አሉ።


 


“ሁለተኛ እንዳይለመዳችሁ” ተብለው በማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ሳይቆነጠጡም አልቀሩም። ወዲያውም፥ የካፌው በራፍ ላይ “ለተማሪዎች አይፈቀድም” ዓይነት ትኩስ ማስታወቂያ ተለጥፎ ነበር።


 


ይኸው ባለፈው ወር የመምህራን ደመወዝ መጨመሩን ሰምተን


 


“እኛ ማስተማር ስናቆምማ የማይሻሻል ነገር የለም” የሚል ቅናት ባይሸነቁጠንም፥…[image error]


 


መንግስት የሆነ ያህል መቶ ብር “ጨመርኩ” ያለ ጊዜ፥ ከወሬው እኩል፥ የቤት አከራዮቻችን የጨመሩብን ብር ትዝ ብሎኛል። በዚያ ሰሞን ነጋዴዎች እንዴት እንዴት እንደሆኑም አይረሳኝም።


 


እና ጓዶች ጭማሪው ከወጪ ቀሪ እንዴት ነው?


 


ከተማሪ ጋር ያጋፋል?


 


የተማሪን የምግብ ምርጫ ያስቀምሳል?


 


የገቢ ግብር ማሻሻያ አዋጅም ከሀምሌ 1 ጀምሮ በሚገኝ ገቢ ላይ ተፈጻሚ እንዲሆን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባስቸኳይ በጠራው ስብሰባ ላይ አዋጅ አጽድቋል አሉ። ምን አስቸኮላቸው?[image error]


 


በነገራችን ላይ፥ ዜናው ላይ የተዘገበው ከቅጥር እና ከኪራይ ለሚገኙ ገቢዎች ነው። ከንግድ ስለሚገኙ ገቢዎች የተባለ ነገር የለም። የተጨማሪ እሴት ታክሱ እንደው ዞሮ ሸማቹ ላይ የሚጨመር ነውና በተዘዋዋሪ ተቀጣሪውን ነው የሚመለከተው። #Ethiopia



ሰላም!

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 26, 2016 20:07

July 19, 2016

ከመንግስት ደጋፊዎች ጋር ያለብኝ ችግር፥

ኢአዴግን ስለሚደግፉ ነው?


አይደለም!


 


በፖለቲካ ዝንባሌያቸው ወይም በገዢው ፓርቲ አባልነታቸው ነው?


አይደለም!


 


ይልቅስ፥


ደጋፊነታቸውን ተጠቅመው ግፍንና በደልን ማውገዝ ቀርቶ፥ እንዳልተፈጸመ ሁሉ ችላ ስለሚሉ ነው!


ሁሉን ነገር በዘረኝነት መነጽር ተመልክተው፥ “ወገኔን የነካ ይነካ” ስለሚሉ ነው!


በአባልነታቸውና የደጋፊነት ጠባያቸው የተነሳ ብቻ ጥቅማ ጥቅሞች ሲደረጉላቸው ተስገብግበው ሆዳቸው ውስጥ ስለሚከቱ ነው!


በፖለቲካ ተሳትፏቸው ተመዝነው በምሁራን ላይ ሳይቀር ህልቅና ሲሰጣቸው ትንሽም ሸምቀቅ ሳይሉ በአምባገነንነት ለመሰልጠን ስለማይፈሩ ነው!


መንግስትን ቅዱስ ስለሚያስመስሉ ነው!


የምንኖረውን የኑሮ ዓይነት አገላለጽ ሊያስተምሩን ስለሚፈልጉ ነው!


አገሪቱ ከእድገትና ልማት ውጭ ምንም ችግር አይወራባትም ስለሚሉ ነው!


የሀሳብ ጥልቀትንና የአነጋገር ብስለትን መጠንከር ስለሚፈሩ ነው!


ለማይረባ ጥቅም ብለው ወዳጆቻቸውን አሳልፈው ስለሚሰጡ ነው!


መንግስትን የቤተሰብ ጉባኤ ስለሚያምታቱትና ተቃዋሚዎችን ሁሉ ጠላት እና ፀረ ሰላም ስለሚያስመስሉ ነው!


ትግሬ ሁሉ ኢህአዴግ፣ ኢህአዴግም የትግሬ ብቻ (mind you, ሕወአት አላልኩም።) እንደሆነ ለማስመሰል ስለሚኳትኑ ነው!


አገሩም የመንግስትና የደጋፊዎቹ ብቻ እንደሆነ ስለሚያምኑና፣ በዛቻ፣ በማስፈራሪያ እና የተለያየ ዓይነት ጥቃት በመፈጸም ሊያሳምኑን ስለሚታገሉ ነው!


በገዛ አገራችን ላይ ሁሉን ነገር እኛ ብቻ እናውቅላችኋለን ስለሚሉ ነው!


ወዘተ!


—–
ሕዝብ እንደው “በቃን!” ካለ ሰንብቷል! ምናለ በከንቱ ከመውተርተርና ሕዝብ ከመፍጀት እነሱም ገገማነቱ እና በውሸት ቅንብር መባዘኑ ‪#‎በቃን‬ ብለው በሰላሙ ቢወያዩና ልባቸውን መልሰው ስህተቶቻቸውን ስለማረም ቢያስቡ? በዘውግ ፌደራሊዝም ስም የዘሩትን እያጨዱ ነው። አሁን “ጆሮ ዳባ ልበስ” ብለው ኖረው፥ በማለቅለቅ ላይ ያሉ ጥቅመኛ ኮካዎች እና ሹመኞች ሁሉ የሰብዓዊ መብት ታጋዮች ሆነው መጥተዋል። ግን ምስኪኑን ሕዝብ በግፍ ማጨዱን ቢያቆሙ ምናለ?



የዘረኝነት አስተሳሰብ ይውደም!


 


#Ethiopia 

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 19, 2016 10:17

July 10, 2016

የወዳጅን ሞት ሰምቼ ስባዝን…

ማኅበራዊ መዋቅራችን አጓጉል ነው። ከደስታ ይልቅ ኀዘንን ለማስታመም ይቀለናል። ከእልልታ ይልቅ ለከንፈር መጠጣ የሚያፈጥነን ይመስላል። በሰው ደስታ ከምንደሰተው ይልቅ፣ ሰዎችን ለተሻለ ፍላጎታቸው ከምንገፋቸው ይልቅ፣ በኀዘናቸው የምንማቅቀው ይበዛል፤ ከፍላጎታቸው ምንገፈትራቸው ይልቃል። በደግ ቀን፥ ስም ስንሰጣጥ፣ ስንፈራረጅ ነው የምንውለው። ደሞ ትንሽ ችግር ሲደቁሰን፥ “ወንድሜ እህቴ” ስንባባልና ስንረባረብ ለጉድ ነው የምናስቀናው።


 


ለምሳሌ፥ አይበለውና እግሬ ቢቆረጥ ሳር ቅጠሉ ያዝናል። ያየ የሰማም ከንፈር መምጠጡ አይቀርም። ደግሞ፥ ይበለውና ዘናጭ መኪና ብገዛ በጣም ጥቂቶች ናቸው የደስታዬ ተካፋይ የሚሆኑት።


 


ከማስታውሰው…


 


ሳልጠይቀው፣ አንድም ቀን… ‘ሞካሪ’ እና ‘የትርፍ ሰዓት ሞንጫሪ’ ነኝ እንጂ፥ አፌን ሞልቼ እንደ ማዕረግ (title) እንኳን ‘ጸሐፊ’ ነኝ የማልልበትን ጉዳይ አንስቶ ሲያንቆለጳጵሰኝ የኖረ ሰው፣ የሆነ ቀን… ከጀርባዬ በመጻፍ ባህርዬ የተነሳ፣ በክፉ በደግ ሲያነሳኝ ከርሞ፣ የሰማሁ ሲመስለው ደግሞ፥ ነገሩም ውኀ እንዲያነሳለት እኔን ማጣጣልና ማንቋሸሽ ተጨማሪ ሥራው ያደርገዋል።


 


“ይሄን ያህል ምን አጠፋሁና ነው? እርሱ ቦታ አልሄድኩ። ሀሳቡን ካፉ ነጥቄው አልጻፍኩበት። መጻፍ እንደው ክህሎት (skill) ነውና፥ ፍላጎቱ እና የተወሰነ ተሰጥኦው ካለ ያድጋል። ደግሞ ባይሆንስ፥ እኔ ሀሳቤን ብገልጽና ያመንኩበትን ብናገር ኑሮውን አላዘባርቅበት። “በርታ…ይሄን ደግሞ እንዲህ አሻሽለው” ቢል ምናለ?” ምናምን እያልኩ ከራሴ ጋር አወራ እና እተወዋለሁ።


 


እሱ አይተወውም።


 


ሌላ ላስታውስ…


 


ስለ ሥራ ማጣት እየተወራ ነው። እኔም ሥራ ፍለጋ ላይ ነበርኩ። የደረሰባችሁና የደረሰላችሁ እንደምታውቁት፥ አብዛኛው ሥራ በዝምድና እና በፖለቲካ አቋም ሁኔታ ነው የሚወሰነው።


 


ከወዳጆቼ ጋር ሰብሰብ ብለን፥ እኔም የራሴን ልምድ ተናገርኩ። “ለስንትና ስንት ጊዜ የሥራ ማመልከቻ ባስገባም፥ ማንም ጠርቶኝ አያውቅም። ግን…” አልኩ። ሲስተሙንም መኮነኔ እና ምሬቴን መግለጼም ጭምር እንጂ፥ በዋናነት ስለራሴ ማውራቴ፣ ወይም የሚታዘንልኝን ናፍቄም አልነበረም።


 


“ግን” ያልኩበትን አፍም ሳልሰበስብ፥ “ኦህ… እንደዛ ነው እኮ። ምን ታረገዋለህ?” ምናምን ተባለ። ወዲያውም “ወዳጄ” የምለው ሰው፣ ለኪነጥበቡ ቅርብ የሆነ (እንደመፍትሄም ጭምር መሆኑ ነው) “ግን ለምን ጽሁፉን seriously አትወስደውም። የሙሉ ጊዜ ጸሐፊ ብትሆን ነው ሁሌ የማስበው። በእጅ ያለ ወርቅ አታርገው። እንግሊዘኛም ጥሩ ነህ። You know, እንደዛ ቢሆን እኮ…”


 


እንደማላደርገው ስለማውቅ፥ “ኧረ እኔ እኮ ለሙሉ ጸሐፊነት የሚያበቃ አቅሙ የለኝም። ጭራሽ እንግሊዘኛ።” ምናምን ብዬ ላሽ አልኩት።


 


የእርሱን ምክር ጋብ አድርጌ፥ “ግን ተመስገን ነው! እስካሁን የምሰራው አላጣሁም። በራሴው ጥረት ተነጋግሬ እና ተደራድሬ በተሻለ ደመወዝ ነው የምሰራው። እኔው ነኝ እንዲቀጥሩኝ የማግባባው። ነገሩ ይገርማል እንጂ ምንም አላጣሁ።” ስል፥


 


“እስኪ ስለራስህ ሌላ ሰው ያውራ።” ብሎ ኩም ሊያረገኝ ይሞክራል። (በጣም ግልጽ ከሆነ ነው ይሄ።) ካልሆነ ደግሞ፥ “ኡፍ እሱ ደግሞ ጉራው መከራ” ምናምን ተብዬ ጫት ማባያ እና ቡና ማጣጫ እሆናለሁ።


 


“ቆይ ግን እኔው ራሴ ስለተንከራተትኩትና ስላወጣሁት ጥረት ማን ነው ማውራት ያለበት? ራሴን ሸጬ ሳበቃ አሻሻጤን በተመለከተ ልምድ ቢቀስምስ እርሱ ነገ የኔን መንገድ ተከትሎ በተሻለ ዋጋ ለተሻለ ቦታ ራሱን ይሸጥም አልነበር? እሱም ቢቀር ስለሆነልኝ ባመሰግንስ ምን አለ? ወይስ ወዳድቄ ሥራ ፈትቼ ብኖር ደስ ይለው ነበር? ስንገርም” ብዬ ተውኩት።


 


ኖርን ኖርንና… በራሴ ገንዘብ፣ በራሴ ትርፍ ጊዜ የጫርኳቸውን ሰብስቤ መጽሐፍ ማሳተሜን ተከትሎ፥ “ኑ ጸበል ቅመሱ” ብዬ የምረቃ ድግስ መጥራቴ ሲወራ፥


 


“አበደ ፈረሴ” አለ። ከጀርባዬ ዘለዘለኝ። ሚስቱን እንደቀማሁበት ሁሉ ጉዳዩ እኔው ሆንኩኝ። አንዳች አገራዊ ጉዳይ እንደተስተጓጎለ ሁሉ በየሄደበት፣ በየወዳጆቻችን ፊት አማኝ። የአጻጻፌን አስጸያፊነትና የባህርዬን መጥፎነት አተተ። አልሰማሁትም እንጂ፥ ወላ “ይቅርብህ” ሊለኝም ዳዳው። …እንግዲህ በትርፍ ሰዓት የሞከርኩትን የማያደንቅ “ወዳጄ” ነው “የሙሉ ሰዓት ጸሐፊ ሁን” ሲለኝ የነበረው።


 


“ምነው ይሄን ያህል፥ ግፋ ቢል ያለመነበብ እጣ ፈንታ ቢገጥመኝ፣ ወይ ደግሞ ጥሩ መጽሐፍ እንዴት እንደማይጻፍ መማሪያ ብሆን ነው እንጂ… የአገር ሀብት መዝብሬ አላሳተምኩ። እሱ ግን ብዋረድ ብቻ ነው ሚደሰተው?” ብዬ ሥራዬን ቀጠልኩ።


 


ፕሮግራሙ ያማረ ሲሆንም፥ እንዲህ ሆነ።


 


ተነቦ ገንቢ feedback ሳገኝም፥እንዲህ ሆነ።


 


አያርገውና፥ “ተበድሬ አሳትሜው ነበር። እና ሙሉ ለሙሉ ከሰርኩኝና የሰው ገንዘብ እንዴት እንደምመልስ ቸገረኝ።” ብለው ኖሮ፥ እርግጠኛ ነኝ “እናዋጣለት” ባይልም ገንዘቡን መልሼ የማገኝበትን መንገድ ለመጠቆም ይሞክር ነበር።


 


‘እንዲህ ያለውን ነገር ብናሻሽል የተሻለ እንኖርና ኀዘናችንም ይቀል ነበር’ እላለሁ።


 


====


 


አቡኪ ሞት ሰቅጥጦኝ ስባዝን ነው ‘randomly’ ይሄን ይሄን የማስበው።



ብልጭ ድርግም አለ። በወጣትነቱ ሄደ። ሞት አዲስ ሆኖ በመጣ ቁጥር ቢያስደነግጥም፥ ነገም እንዲሁ ነን እኛ።


ነፍሱን በአጸደ ገነት ያኑራት!


13342971_646994268791366_2197683848191752176_n



ልበ ቀናው ወዳጃችን ይህ ነበር። :'( 

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 10, 2016 11:25

July 8, 2016

የሁለት ዓለም…

አብሮ መኖር ማለት፥


“ተማርጦ መሻለም”፣ “መርጦ ማየት” ማለት፣ ሆኖ ተቸግረን፣


አለን……. ከአንድ የአበባ ማሳ እኩል ተበትነን፤


 


እናንተ ቀንቷችሁ፥ አበባ መርጣችሁ፣ አበባ ስታዩ፣


ከቀለም ቀለሙ፥ ስትቀጥፉ ከቢጫው፣ ስትቀጥፉ ከቀዩ፤


 


እኛ ግንድ ለግንድ (በምን ያል እርግማን) ከእሾህ ስንታከክ፣ ሲያቆስለን ስቃዩ…


ከአበባ ማሳ ላይ በኬሚካል ብዛት ጤናውን እያጣ፣


_ለቁጥቁጥ ደመወዝ፣ ለኩርማን እንጀራ፥ የሰው ልጅ ባታዩ፣


ምስኪኑ ገበሬ፥ በገዛ መሬቱ በጨፈቃ ተመን፣ “ካሳ” ተቆርጦለት


ቱጃር ካንጣለለው የአበባ እርሻ ላይ በ“ጥበቃ” መደብ ከበራፍ ላይ ዋዩ…


ጎልተው እየታዩን ከቀለማት ደምቀው፣ ከጽጌያት ልቀው፣


መልካት አፈትልከው፣ በግፍ መሀል ወጥተው፤


 


እናንተ ከማሳው ባገኛችሁት ሲሳይ፣ በአበባ አጀባ፣


ከምስኪን ሴት ልብ ውስጥ ልባችሁ ሲገባ፣


በምናብ ሲሰመር፥ አንሶላው ሲፈረሽ፣


(ስጋ ነፍስ ሲለያይ፣ ትራስ ተንተርሶ)


በስሜት ሲቀመር፥ “ሰበረልዎ” ሲዜም፣


(ሰባራ እንኳን ቢሆን በምላስ ታድሶ)


 


እኛ እናስባለን የሰቀቀን ዜማ፥


በአበባዮሽ መሀል የተሰነቀረ፣


_በአበባ ተከ’ቦ፣ በናፍቆት ሚሰማ


 


“እንኳን ቤትና የለኝም አጥር፣


እደጅ አድራለሁ ኮከብ ስቆጥር”


 


ስትል ባታይቱ፣


ጊዜ እና ጊዜያዊ ገሸሽ ያደረጓት፣ ባለመሬቲቱ።


 


“ንፍሮ ቀቅዬ ብላ ብለው


ጉልቻ አንስቶ ጎኔን አለው”


 


ስትል ምስኪኒቱ፣


የባለስልጣኑ፣ የባለጉልበቱ፣ ታማኝ ባለቤቱ።


 


ጆሯችን ይገባል፣ እናዳምጣለን፥


ምርጫ ተቸግረን፣ ተረግመን! ተለክፈን!


 


/ዮሐንስ ሞላ/

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 08, 2016 16:14

July 7, 2016

ወፌ ወፌ ላላ

ተራማጁን ጥሎ. . .


አጥንቱን ረብርቦ፣ ሥጋውን ደልድሎ፣


ተራማጁን ይዞ. . .


እግር ከወርች አስሮ፣ ካ’ለም በቃኝ ዱሎ፣


ይገነባል ሌላ፤


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ይውላል ሲያሽላላ፣ ሲገርፍ ያንን ገላ፤


ያንን ለጋ ብልት፣ ያን ልስልስ ሰውነት፣


ያንን ጉስቁል ዛላ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ተራማጁን ጠምዶ፣


ከጎጆው አሳ’ዶ፣ ከሰው ቀዬ ጥሎ፤


ድንጋዩን ፈንቅሎ፣ አፈሩን ፈልፍሎ፣


መንገዱን ጠርቅሞ፣ ይቀይሳል ሌላ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ሕያዉን አባርሮ፣ ግዑዝ ይቆልላል፣


ታዛውን ጠርምሶ፣ ሌላ ይቀልሳል፤


አለት ይከምራል፣ አፈር ያላቁጣል፣


ይህን አፈናቅሎ፤ ያንን ያሳፍራል፣


ጠርሙስ እየፈጨ፣ ጠርሙስ ይጋግራል፤


ኑሮውን ጠርምሶ፣ ሰዉን አፈናቅሎ. . .


ሌላውን ያሰፍራል፣ ቋሚውን መንግሎ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ጎጆሽ የቆመበት፣ የታል ያንቺ ባላ?


የታል ቅርንጫፉ? የቤትሽ ከለላ?


ስንጥር፣ ዝንጣፊው? የማደሪያሽ ጥላ?


የታል መጋረጃው፥ – የጓዳሽ ከለላ?


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ለእኔ ይተርፋል ብዬ የተመካሁበት


ቢጋርደኝ ብዬ፥ ቢያስጥለኝ ከበላ፣


ቢያተርፈኝ ካውላላ የተጠለልኩበት


የማደሪያሽ ጥላ፤


የታል ያንቺ ባላ? የታል የእኔ ገላ?


የታል ያ ሰውነት? – ሰዉን አጫራሹ፣


– ጎጆ አስቀላሹ፣ አብራሪው በራሪው፥


– አፍራሹ፣ አዳሹ፥. . . ያ ዘንካታ ገላ?


የታል ያ ዝማሬ? የታል ያ ቅላፄ? የታል ያ ሽለላ?


 


ወፌ ወፌ ላላ፥


 


ብር በይ ወደ እኔ፥ (እንዲህ ተጎሳቁለሽ) ወፍ ሳያይሽ ሌላ፣


የቃረምሽው ካለ፣ ማዕድ እንካበብ፣ ነይ አብረን እንብላ።


ከሌለም እንተኛ፣ – ተቃቅፈን እንጥፋ፣


– እስክንነቃ ድረስ፣ ሌሊቱ እስኪገፋ፣


እናንጋ፥ ባንድ አልጋ! እናውጋ በይፋ!


እየቋጨን አምሮት፣ እየቋጠርን ምኞት፣ እየሰፋን ተስፋ፣


እንዲህ እንጨዋወት. . .


ወፌ ወፌ ላላ. . .


እስከጊዜው ድረስ፥ እስኪመታ መላ፣


ይኸኛው ተገፍቶ፣ እስኪተካ ሌላ!


 


/ዮሐንስ ሞላ (2008) “የብርሃን ሰበዞች” ገጽ 64 – 65/

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 07, 2016 16:15

ዮሐንስ ሞላ's Blog

ዮሐንስ ሞላ
ዮሐንስ ሞላ isn't a Goodreads Author (yet), but they do have a blog, so here are some recent posts imported from their feed.
Follow ዮሐንስ ሞላ's blog with rss.