ወፌ ወፌ ላላ

ተራማጁን ጥሎ. . .


አጥንቱን ረብርቦ፣ ሥጋውን ደልድሎ፣


ተራማጁን ይዞ. . .


እግር ከወርች አስሮ፣ ካ’ለም በቃኝ ዱሎ፣


ይገነባል ሌላ፤


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ይውላል ሲያሽላላ፣ ሲገርፍ ያንን ገላ፤


ያንን ለጋ ብልት፣ ያን ልስልስ ሰውነት፣


ያንን ጉስቁል ዛላ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ተራማጁን ጠምዶ፣


ከጎጆው አሳ’ዶ፣ ከሰው ቀዬ ጥሎ፤


ድንጋዩን ፈንቅሎ፣ አፈሩን ፈልፍሎ፣


መንገዱን ጠርቅሞ፣ ይቀይሳል ሌላ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ሕያዉን አባርሮ፣ ግዑዝ ይቆልላል፣


ታዛውን ጠርምሶ፣ ሌላ ይቀልሳል፤


አለት ይከምራል፣ አፈር ያላቁጣል፣


ይህን አፈናቅሎ፤ ያንን ያሳፍራል፣


ጠርሙስ እየፈጨ፣ ጠርሙስ ይጋግራል፤


ኑሮውን ጠርምሶ፣ ሰዉን አፈናቅሎ. . .


ሌላውን ያሰፍራል፣ ቋሚውን መንግሎ፣


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ጎጆሽ የቆመበት፣ የታል ያንቺ ባላ?


የታል ቅርንጫፉ? የቤትሽ ከለላ?


ስንጥር፣ ዝንጣፊው? የማደሪያሽ ጥላ?


የታል መጋረጃው፥ – የጓዳሽ ከለላ?


ወፌ ወፌ ላላ. . .


 


ለእኔ ይተርፋል ብዬ የተመካሁበት


ቢጋርደኝ ብዬ፥ ቢያስጥለኝ ከበላ፣


ቢያተርፈኝ ካውላላ የተጠለልኩበት


የማደሪያሽ ጥላ፤


የታል ያንቺ ባላ? የታል የእኔ ገላ?


የታል ያ ሰውነት? – ሰዉን አጫራሹ፣


– ጎጆ አስቀላሹ፣ አብራሪው በራሪው፥


– አፍራሹ፣ አዳሹ፥. . . ያ ዘንካታ ገላ?


የታል ያ ዝማሬ? የታል ያ ቅላፄ? የታል ያ ሽለላ?


 


ወፌ ወፌ ላላ፥


 


ብር በይ ወደ እኔ፥ (እንዲህ ተጎሳቁለሽ) ወፍ ሳያይሽ ሌላ፣


የቃረምሽው ካለ፣ ማዕድ እንካበብ፣ ነይ አብረን እንብላ።


ከሌለም እንተኛ፣ – ተቃቅፈን እንጥፋ፣


– እስክንነቃ ድረስ፣ ሌሊቱ እስኪገፋ፣


እናንጋ፥ ባንድ አልጋ! እናውጋ በይፋ!


እየቋጨን አምሮት፣ እየቋጠርን ምኞት፣ እየሰፋን ተስፋ፣


እንዲህ እንጨዋወት. . .


ወፌ ወፌ ላላ. . .


እስከጊዜው ድረስ፥ እስኪመታ መላ፣


ይኸኛው ተገፍቶ፣ እስኪተካ ሌላ!


 


/ዮሐንስ ሞላ (2008) “የብርሃን ሰበዞች” ገጽ 64 – 65/

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on July 07, 2016 16:15
No comments have been added yet.


ዮሐንስ ሞላ's Blog

ዮሐንስ ሞላ
ዮሐንስ ሞላ isn't a Goodreads Author (yet), but they do have a blog, so here are some recent posts imported from their feed.
Follow ዮሐንስ ሞላ's blog with rss.