ዮሐንስ ሞላ's Blog, page 12

January 30, 2017

የሁለት ፕሮፌሰሮች ወግ…

 “ከቤተሰቤ መካከል አማርኛ የምችል እኔ ብቻ ነኝ።[image error]

ሌሎች 13 ወንድምና እህቶቼ አማርኛን እንዳይሰሙም

እንዳይናገሩም አድርገን በጥሩ ሁኔታ አሳድገናቸዋል።

አሁን ያለዉ የቁቤ ትዉልድም ከሞላ ጎደል አማርኛን

የማይናገር የማይሰማ ጀግና ትዉልድ ሆኗል።”


~ ፕ/ር ህዝቅኤል ጋቢሳ (በOMN)


[image error]


“ቋንቋን በአግባቡ ያለመጠቀም የኦሮሞ ሕዝብ ተገቢ የመብት ጥያቄዎችን ለሌሎች እንዳያስረዳ እንቅፋት ከሆኑበት ነገሮች አንዱ ይመስለኛል፡፡ በ1983ቱ የሽግግር ጉባዔ ላይ እነ ኦቦ ሌንጮ ለታ ለየት ለማት በአስተርጓሚ ለመናገር ሲሞክሩ፣ አቶ መለስ በመንዝአማርኛ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሲፈልጥና ቆርጦ ሲቀጥል ነበር፡፡ ፓለቲካ ለሚያውቅና ለገባው ሰው፣ ኦሮሚፋ አንድ ቀን እንኳ በአደባባይ ይሰማልን የሚባል የአናሳ ቡድን ቋንቋ ሳይሆን ትልቁ የኢትዮጵያ ብሄር የሚናገረው ቋንቋ ነው፡፡ ሙዚየም ውስጥ ይቀርብኛል ተብሎ የሚሰጋለት ቋንቋ አይደለም፡፡ የቋንቋ ፖለቲካ የማይናቅ ባይሆንም፣ በተገቢው ጊዜና ቦታ ካልተጠቀሙ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል፡፡”


~ ፕ/ር መረራ ጉዲና – “የኢትዮጵያ ፓለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የሕይወቴ ትዝታዎች ከኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ እስከ ኢህአዲግ” ገፅ 225


ቋንቋ


መግባቢያ ነው። ክህሎት እንጂ እውቀት አይደለምና ባይችሉ አያሳፍርም። መቻሉም ቢያስደንቅና ቢጠቅም እንጂ፥ የተለየ ሆኖ የሚያስኮፍስ ነገር አይደለም። ሰው እንደዋለበትና እንደፈለገው ልክ የትኛውንም ቋንቋ ማወቅና በአግባቡ የመጠቀም ክህሎቱን ማሻሻል ይችላል። ብዙ ቋንቋ ባወቀ ቁጥር ግን የተሻለ መግባባት እና መፍትሄ ማምጣት ይችላል።


በተለይ፥ ቋንቋውን ሆነ ብሎ ላለመማር መጣርም ጉልበትና ጥረት ይጠይቃልና ራሱን የቻለ ድካም አለው። ማለዳ ማለዳ ተነስቶ፥ ልጆችን ስለጥላቻ መስበክ፣ እሱን ቋንቋ እንዳትናገሩ ብሎ መጨቆን፣ ጓደኞቻቸውን መምረጥ፣ ውሏቸው ላይ ጣልቃ መግባት… ሁሉ የመብት ጥሰቶች ሆነው ያስወቅሳሉ እንጂ፥ እንደጥሩ ገሪነት የሚያስደንቁ አይደሉም። ወላጅ/አሳዳጊ ከዚህ በላይ ሊበድልም አይችልም!


እኔ ኦሮሚኛ ለመማር ከምደክመው በላይ (አዲስ ቃል ብሰማ እና አፌ ውስጥ ቢገባ ለመጠቀም እደጋግመዋለሁ እንጂ ስለመርሳት አልጨነቅም) እነ ፕሮፌር እዝቅሔል ቤተሰብ ልጆቻቸው አማርኛ እንዳያውቁ የደከሙት ሲታሰብ ያስቆጫል። ልጆች ከሰው ጋር ተግባብተው እንዳይኖሩ መፍረድ ኅሊና ላለው ሰው ግፍ ነው።


በክልልስ እሺ፥ መንግስትም ለይስሙላ ፌደራሊዝሙ ሲል “በአፍ መፍቻ ቋንቋ አስተምራለሁ” ይላልና በዚያ ያልፋሉ። 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ሲመጡ መግባባት ከባድ ይሆናል። ዩኒቨርስቲ ሲገቡም እንዲሁ ሆኖ ሰው ባያገል እንኳን ራስን ማሸሽም ይከሰታል። ሕብረተሰብ ካልተግባባ ደግሞ ግፈኞች ጥሩ ምሽግ ያገኛሉ።


ስለታሪክስ ቢሆን በአንድ ቋንቋ እና ወገን ብቻ የተነገረውን፣ እንደዶግማ ከመጋት፣ ብዙ ማስረጃዎች (resources) ያሉበትን ቋንቋ፥ “ላስተምር” ብሎ መጣር ቢቀር፣ “እንዳይማሩ” ብሎ መነሳት ክፋት እንጂ ሌላ ምን ምክንያት አለው?


በአሜሪካ


[image error]ፕሮፌሰሩ እዝቅሔል ገቢሳ፣ ካለክልሉ አስጠግታው፣ ቤት ንብረት አፍርቶ፣ “ሰዎችን ከክልላችን ውጡ” እያለ እንደልቡ እየተከፈተ በሚኖርባት እና በሚያስተምርባት አገረ አሜሪካ…


ሰሞኑን የሜሪላንድ የጤና መድኅን ዋስትና ማዕከል፣ ለደንበኞቹ የላከው ደብዳቤ ላይ ወደ 17 የሚጠጉ ቋንቋዎች (Bassa የሚባል ስሙን ሰምቼው የማላውቀው እና፣ ‘Khmer’ እና ‘Laotian’ የሚባሉ ቋንቋዎች፥ ፊደሎቻቸው እርስበርስ ተያይዘው ሸረሪት ቀለም ነክታ ወረቀቱ ላይ የሄደችበት መስለው የሚያስቁ ሳይቀሩ ተካተው) ተጠቅሞ ያስተላለፈውን መረጃ ተመልክቼ ነበር። ከቋንቋዎቹ ውስጥ፥ አማርኛ እና ኦሮሚኛም ተካተውበታል።


በአማርኛ የተጻፈው….


“ያለምንም ክፍያ በራስዎ ቋንቋ እገዛ የማግኘት መብት አለዎት። ስለማመልከቻዎ ወይም ከጤና ዋስትና ድርጅቱ ስለሚያገኙት ሽፋን ማንኛውም ጥያቄዎች ካሉዎት፣ ወይም ይህ ማሳወቂያ በግልፅ በተጠቀሰ ቀን ማድረግ ያለብዎ ነገር እንዳለ የሚያስገድድዎ ከሆነ፣ በተጠቀሰው የስልክ ቁጥር ለስትቴትዎ ወይም ለክልልዎ ደውለው ከአስተርጓሚ ጋር ይነጋገሩ።” ይላል።


[image error]አሜሪካ ውስጥ፣ ከቆሻሻ መጣያ ቅርጫቶች አንስቶ በተለያዩ ቦታዎች፥ የአማርኛንም ሆነ ሌሎች ቋንቋዎችን ተጠቅመው ለመግባባት ሲጥሩ ይታያል። በሂደቱ፥ የሚያስቁ አጠቃቀሞችም አይጠፉም።


ከገጠሙኝ መሀል፣ በ’ዋሽንግተን ኤቲካል ሶሳይቲ’ አዳራሽ መጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ “Do not put paper towels in the toilets.” የሚለውን መልእክት በ5 የተለያዩ ቋንቋዎች ለማስተላለፍ ሙከራ ተደርጓል። በአማርኛ የተጻፈውን ስመለከተው፥ “ዶ ኖት ፑት ፓፐር ቶወልስ እን ቶእለፅ!” ይላል።

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on January 30, 2017 09:56

January 14, 2017

Good news…

[image error]The long waiting and imploring have come to an end, finally! The cruels banned what shouldn’t be banned in the first place, – ‘traveling for better medication’, even traveling for leisure would have been up to the individual… now, they have ‘allowed’ and we’re happy that Habtamu Ayalew is safe in USA. This is an ever ugly drama: ‘they take our rights’, and when they give us back, ‘we celebrate’.


But if one can afford, why not even to the Mars, even to the Moon? What the hell should the government get to do with it? But this is how it is when ‘gun’ governs… it even would have been worse.



Hallelujah! And congrats for all who have been concerned. And all the best Habtish and family!


—-


Habtamu Ayalew, has beenformer spokesman of the opposition, Andenet (Unity), Party, and he was arrested on July 8, 2014 and charged with ‘terrorism for allegedly collaborating with the opposition Ginbot 7’, which the Ethiopian government has proclaimed as ‘a terrorist group’. Habtamu was detained at the notorious Maekelawi and Qilinto Prisons, where he was subjected to torture and other ill-treatment through denial of access to toilet facilities, ‘a situation that led to him to develop excruciatingly painful hemorrhoids’. He was banned from leaving the country because the prosecutor has appealed the ‘release from prison’ decision of the High Court. As known, his hemorrhoids were easily treatable, hadn’t it been left untreated to get worse to stage 3. 


 


 



 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on January 14, 2017 15:21

የማንሳት ኃይል

እደጃፌ ወድቆ


ሳየው ኑሬ ኑሬ


ወዳጄ ሲያነሳው፣ ውድነቱን አውቆ


በንፍገት ደንብሬ፥


ልቤ ሊያብድ ተጨንቆ፣


ነፍሴ ሊበር ወልቆ፣ ስጋዬን አሳቅቆ።



እደጃፌ ወድቆ


“ለእግዜር” እንኳ ባልል፣


ለዐይኔ ተቆርቁሬ


ሳላነሳ ትቼው፣


ሲንደፋደፍ ከእግሬ


የቀረን ምስኪን ሰው


ስለነፍስ ያደረ ሳምራዊ ሲያነሳው፥


መጽደቁን ቆጥሬ፣


የደጉን ተጋድሎ፣ ባገር መወደሱን


በሀሳቤ ዘርዝሬ፣


በቁጭት ተቀጣሁ፣


ዋልኩኝ ተንጨርጭሬ


በክፋት ደንብሬ፣ በቅናት ታጥሬ።


* * *


ነገር ግን ይገርማል!


 


ወዳጅ ባየው ቅጽበት


ባነሳበት አፍታ፥


በተመኘው ጠዋት፣


ባጌጠበጥ ማታ፥


የጣሉት ይከብራል


ዋጋው ይጨምራል።


* * *


ጥፍጥናዬን ምጎ፣ መረቄን ጨርሶ


ከአውላላ ሜዳ ላይ የተፋኝ አንኳሶ፥


ስደክም የዘረረኝ፣ ስወድቅ የረገጠኝ


ስንከራተት ደጁ፣ ያልጣለልኝ ከእጁ


ያልነበርኩ ወዳጁ፥ ቆለለኝ ስነሳ


ካበኝ በየፈርጁ፣ ሰፈረልኝ ካሳ።


* * *


ለካስ ለመላ ነው የሚለው አገሩ፥


“የወደቀን አንሱ፣ የሞተን ቅበሩ”


ካለፈ እንዲማሩ፣ በወግ እንዲኖሩ


እጃት እንዲጥሩ፣ ዐይናት እንዲበሩ።


 


/ዮሐንስ ሞላ/

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on January 14, 2017 15:08

December 19, 2016

May God be with you all and other victims!

[image error]


 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on December 19, 2016 15:28

December 18, 2016

ምስጋና እና ብርታት

የሰው ልጅ ብቻውን እንደሆነ እንዳይሰማው፣ እንዳይሰለቸውና እንዳይፈራ በነገሩ ሁሉ በዓላማ መኖሩን እንዲያውቅና እንዲረዳ፣ ፈጣሪ ዓይኖቹንና ጥርሶቹን አጎራበታቸው። ዙሪያውን በሰው ልጆች አጠረው። ስሜቶቹን አሰለፈለት። ጊዜንም በወቅት ከፋፈለ: ክረምት፣ ፀደይ፣ በጋ፣ በልግ…ጨለማ እና ብርሀን… ጠዋት እና ማታ… እርሻ እና አዝመራ… ኀዘን እና ደስታ። ትዝታን እና ተስፋንም በልቡ አኖረለት። አጢሀት እና ይቅርታንም በመንገዱ ላይ አቆመ። ከአፈርና ከአጥንት እፍ ብሎ የምድርን ጾታ አሰባጠረ። ለዘወትር ድካሙ እንዲሆን፥ ካለአጀንዳም አላስቀረውም።


 


“ፀሐይ ይሁን” ቢል፥ ፀሐይ ሆነ። ጨረቃና ከዋክብትን፣ ነፋስና ውሀንም እንዲህ አፀና። ሥነፍጥረት ሁሉ በቃሉ ተከናወኑ። የሰው ልጅን ከነአስገራሚ መላመዱ እና ከነጥበቡም በእለተ አርብ ፈጥሮ ፍጥረታትን አስገዛለት። መንገድንም አመላከተው። በተሰጠው ላይ የሰው ልጅ እየጨመረበት ነገር ሁሉ ይበልጥ ውብ ሆነ። ፍቅርን ምድር ላይ ዘራ። ስለመኖሩ ምልክት እንዲሆኑት፣ እንዲጽናና እና እንዲበረታበት ለሁሉም አንጻርና ወዳጅ አላሳጣውም። ሲለቀስ ለሲቃ ጥርስ ይነከሳል፣ አፍንጫም ከጥርስ የሚሰበስበው አቅም አለ። ሲሳቅም አይን አብሮ ይስቃል እንጂ የጥርስ ድርድር መታየት ብቻ ሳቅ አይባልም።


 


አዋራና ጎርፍ ይፈራረቃሉ። ህጻናት ያድጋሉ። ወጣትነት ሲሰሰት ያልፋል። ጉልምስና በክፋት፣ በ“ካለ’ኔ”፣ እና በራስ ወዳድነት ይጠቀረሻል። ያልለገሙበት ጊዜ ወራዙት ግን ከራስ አልፎ ዙሪያንም ያበለጽጋል። ልብ የሰበሩለት ጉልምስናም ጌጥ ለሚሆን ሽምግልና ይገነባል። ውብ አበባ፣ ጣፋጭ ፍሬ እና እሾህ ካንድ ዛፍ ላይ ይበቅላሉ። ሁሉም እንደመድረሱ ልክ እና እንደመሻቱ ይለቅማል። ዕድሉ ሆኖ፥ ካማረ መስክ ላይ መጣል የሚቀናው አይጠፋም። ለፍሬ ብሎ ተንጠልጥሎ እሾህ መያዝና መፈተንም አለ። ፀንተው ቢቆዩ ፅናት ወደፍሬው ያሻግራል። ደግሞ ‘እሾህ ነው ዕጣፈንታዬ’ ብለው ቀድመው ሲያማርሩ፥ ፍሬ ታድሎ በረከት መቁጠርም የሰው ልጅ እጣ ፈንታ ውስጥ ይገኛል። እግዚአብሔር “ይሁን” ሲል ግን፥ አንዲት ጀምበር ይበቃል!


 


“ነገር ሁሉ ያደክማል፤ ሰው ይናገረው ዘንድ አይችልም፤ ዓይን ከማየት አይጠግብም፥ ጆሮም ከመስማት አይሞላም።”ና ቆመን መሄዳችን እስኪደንቀን ድረስ በዓይን እና በጆሯችን አሳልጦ የገባ መአት ጉድ እንታጨቃለን። ግን እንኖራለን። ከብዶን የወደቅን እንደው፥ ጉዱም ጉድ አይሆን። …ከእናታችን ማህጸን ጀምሮ ታውቀን እስከራስ ፀጉራችን ድረስ ተቆጥረናል። ይተናነቀናል እንጂ፥ “በእምነት ሆናችሁ ተራራውን ሂድ በሉትና በመደነቅ ኑሩ” ተብለናል።


 


ስሜት ቦታና ጊዜው ሲገጥምለት ጽንስ ይሆናል። እናት ልጇ ቢራብ ጡቷ ላይ ህመም ይሰማታልና በዚያ ታውቃለች። አድጎ፥ እንኳን ህመም፣ ከረር ያለ ግጭት ውስጥ ቢገባ እንኳን ሳይነገራት እንድታውቅ የፈጣሪ ድንቅ ሥራ ነው። ደግሞ ሽል ሳይቀር ድምጽና ወሬ ይለያል። ተክሎችም በሙዚቃ ይፈነጥዛሉ። ጠፉ ሁሉ በልባዊ ፈገግታ ይለመልማል። የተፈጥሮ ዑደት፣ የእጽዋት እና እንስሳት እድገትና መዝናናት፣ የዘመናት መፈራረቅ፣ የወቅቶች ማለፍ፣ የእጁ ሥራ ሁሉ አይጓደልም። ሰው ሲሞት፥“ዋርካው ወደቀ” ተብሎ በሀዘን ቢረገድ፥ ሺህ ዋርካዎች ከሥር ይወለዳሉና በዚያ መጽናናት ይሆናል። “ቆሜያለሁ” ቢሉም መውደቅ አይቀርምና ልብ ብለን ብናይ ማስታወሻው ብዙ ነው። ድንቅ ነው!


 


ተመስገን! ፀሐይና ጨረቃን ሰው አይፈቅድም። ብርድና ሙቀትንም ሰው አይከለክልም። ፍቅርን ሰው “ይሁን… አይሁን” አይልም። ስለዚህ ካለን፥ ምን ሌሊቱ ቢረዝም፣ ሲነጋ ጠዋት መሆኑ አይቀርም። ከቆየን፥ ደመናው አልፎ ፀሐይ ይሆናል። ይኽ እውነት ነው የሚያበረታን!


 


ፍቅርና ማየት ምርኩዝ ሆነውኝ እኖራለሁ። ጭጋጋም ቀናትን ተሻግሬ ብርሃናቱን አቅፍ ዘንድ፣ ዳፍንታም ቀናትም እንዲሸማቀቁ የፈጣሪ ቃል ነውና አይታጠፍም። ደግሞም የቀደመ ልምድ ያበረታል እንጂ፥ ተመልሰው በቦታ እና ጊዜ ለውጥ እንደሚመጡም አውቃለሁና እግዚአብሔር መርሳትን አያድርግብኝ።


 


አሁን ደምና ጦር አስደንግጠው እንደሚያደነድኑት ዓይነት፥ የጠላትም የወዳጅም ቅይጥ መንፈሶች ስንቅ ሆነውኛልና በፍጹም አልፈራም! ለዚህ በሰማይና በምድር፣ ከተጻፈው እና ካልተጻፈው ብዙ ምስክር አለኝ!


 


ሃሌ ሉያ!

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on December 18, 2016 15:30

December 12, 2016

ዝክረ እረፍቱ ለምኒልክ

[image error]«….ማንም ሰው ለመማርና ለመሠልጠን መድከም አለበት።» ~ አፄ ምኒልክ በ፲፰፻፺፰ ዓ.ም ስለትምሕርት ያስነገሩት አዋጅ [ዘውዴ ረታ “ተፈሪ መኮንን – ረዥሙ የሥልጣን ጉዞ” (ውክፔዲያ ላይ እንደተጠቀሰው)]


 


ከአፄ ምኒልክ የአዋጅ ቃል የምረዳው እውነት፥ ማንም ለመጠንከርና ለመሰልጠን ቢፈልግ፥ በቅድሚያ መድከም እንዳለበት ነው። ‘መድከም’ን የተረዳሁት ደግሞ በሁለት መልኩ ነው፤ – የመጀመሪያው፥ ‘መልፋት፣ መጣር፣ መጋር…’ ሲሆን፥ ሌላኛው ደግሞ ‘ድክመትን ማስተናገድና በደካማነት መስመር መጓዝ’ ብዬ ነው። …ብዙ ጊዜ ቁጭ ብሎ ሲሳይና አዱኛ የለም። ድንገት ቢኖር እንኳን፥ እጅና እግርን አጣጥፎ መማርና መሰልጠን፣ ማደግና መሻሻል ሊመጡ አይችሉም።


 


ደግሞም እንደ ጊዜና ሁኔታው ለመማርና ለመሰልጠን በደካማነት መስመር መጓዝ ግድ የሚል ቅድመ ሁኔታ (input) ባይሆንም፥ ሰው በጉዞው መሀል ቢደክም ያ ጤነኛና ማንንም ሊያጋጥም የሚችል ነገር መሆኑን እናውቃለን። ዋናው ነገር ግን የቀደሙት የፈፀሙትን ድክመት/ስህተት እኛ እንዳንደክም ማሰብ ነው። …እነርሱ ከተጓዙበት ጎዳና በተሻለ እኛ መረማመድ የምንችል ስለመሆን መጨነቅ ነው። …የቀደሙት በእሾህ እና በቆንጥር ያጠሩት ጎዳና ቢኖር፥ ደግሞ በመልካም የጠረጉትም ጎዳና አለና፥ በርሱ ገብተን ቆንጥርና ሾህ ያለበትን መንገድ በማፃዳት ለመጪው ትውልድ የተሻለ መንገድ ማበጀት ነው። …እንጂ ታሪክ ለመማሪያና ዛሬን ለማሻሻያ ሳይሆን፥ ዝም ብሎ ለመራቀቅና ጨዋታን ለማሳመር ፍጆታ የሚውል የሚጠቅም አይመስለኝም።


 


የእኛ ሰው፥ ሲወድና ሲያደንቅ የቅዱሳንን ደረጃ ሰጥቶ… የወደደው ሰው ፍፁም የማይሳሳት፣ የሰውነት ግብሮች የሌሉት አድርጎ የመሳል አባዜ ስላለበት፥ አፄ ምኒልክን በሚወዷቸው ሰዎች ልብ ዘንድ እንዳለው የቅዱሳን ደረጃ ሊኖራቸው አይችልም። …ደግሞም እንዲሁ፥ የእኛ ሰው፥ ሲጠላና ሲጠምድ የሰይጣንን ደረጃ ሰጥቶ… የጠላው ሰው ፍፁም የማይረባ፣ ጭራሽ የሰው ልብ የሌለው ተልካሻ አድርጎ የመክሰስና የመውቀስ ዝንባሌም አለና፥ አፄ ምኒልክን በሚወነጅሏቸው ሰዎች ልብ ዘንድ እንዳለው ዓይነት በመጥፎ ሥራ ብቻ የሚታወሱ አይደሉም። ጭራሽ ስማቸውን ለምን ሰማሁ ማለትም ከነውርም አልፎ አደገኛ አላዋቂነት ነው።


 


ዛሬ አንገታችንን ቀና አድርገን ከነድህነታችን በኩራት ቀጥ ብለን የምንራመድበት የአድዋ ድል፥ የአፄ ምኒልክ የመሪነት ውጤት ነው። አዳዲስ ነገሮችን ወደ ሀገር ለማስገባትና ስልጣኔዎችን ለማስተዋወቅ መጣራቸውና በብዙ ማሳካታቸውም አይዘነጋም። ታዲያ እንዲሁም፥ ግዛትን በማስፋትና የሳሉትን የኢትዮጵያ አንድነት ወደመሬት አውርዶ በማስፈፀም ስሜት በርሳቸው የተበደሉ ዜጎችም አሉ። ያ ያለፈ ታሪክ ነውና ዛሬ ላይ መልሰን ማኖር (undo ማድረግ) የምንችለው አይደለም። ‘ይቅርታ እንጠያየቅ አካኪ ዘራፍ’ የሚያስብልም አይመስለኝም። ዛሬ ያ እንዳይደገም መታገል ግን እንችላለን። …የቀደሙት የፈፀሙትን ስህተት በማረም ሽፋን እኛ ደግሞ የከፋውን ስህተት እንዳንፈፅም መጠንቀቅ አለብን።


 


የዛሬ 103 ዓመት በሰላም ያንቀላፉትንና የነበሩበት ስርወ-መንግስት (regime) ያከተመውን መሪ ትተን፥ ዛሬም በሕይወት ያሉ ብዙ በደለኞችና ጨካኞችን የሚያስተዳድሩ ስርዓቶች (systems) ~ መሪውም ተቃዋሚውም ጎራ ~ አሉና፥… ከትናንት ጋር ውኀ ወቀጣ ስንታገል፥ ዘነዘናና ሙቀጫችን ዛሬን እንዳናይ ለራሳችን ደንቃራ እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን። ….ዛሬ የትናንትን ጥፋት በማውገዝና በመቆርቆር ሰበብ ታሪክ እያነሳን እየጣልን ስንወሸክት፥ የከበደውን ጥፋት እንዳንፈፅም ማሰብ ይገባናል። …በጊዜ ወደኋላ ሩቅ ሳንሄድም፥ ዛሬ እየተሰራ ያለውን ታሪክ ነገ ሲፃፍ እንዴት ሊያምርና የሚያስቆጣቸውን ሰዎች ሊቀንስ እንደሚችል በማጤን የራሳችንን ኃላፊነት ስለመወጣት ብናስብ ትርፉ ይበዛል።



«እናንተ አንድ ልብ ከሆናችሁ በምቀኝነት እርስ በርሳችሁ ተዋግታችሁ ካላለቃችሁ በቀር ኢትዮጵያን አገራችንን ለሌላ ለባእድ አትሰጧትም፤ ክፉም ነገር አገራችንን አያገኛትም። ነፋስ እንዳይገባባችሁ አገራችሁን በያላችሁበት በርትታችሁ ጠብቁ፤ ወንድሜ ወንድሜ እየተባባላችሁ ተደጋገፉ፤ የኢትዮጵያን ጠላት ተጋግዛችሁ ተደንበር መልሱ። የኢትዮጵያ ጠላት ባንዱ ወገን ትቶ ባንድ ወገን ቢሄድና ደንበር ቢገፋ፤ በኔ ወገን ታልመጣ ምን ቸገረኝ ብላችሁ ዝም አትበሉ፤ ያ ጠላት በመጣበት በኩል ኁላችሁም ሄዳችሁ አንድነት ተጋግዛችሁ ጠላታችሁን መልሱ እስከ እየቤታችሁ እስኪመጣ ዝም ብላችሁ አትቆዩ» ~ ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ፤ ግንቦት ፲ ቀን ፲፱፻፩ ዓ.ም. (አፈወርቅ ገብረኢየሱስ፣ (፲፱፻፩ ዓ/ም) ውክፔዲያ ላይ እንደተጠቀሰው።)


 


ዝክረ እረፍቱ ለምኒልክ ❤ !


ነፍስህን በገነት ያኑራት!

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on December 12, 2016 15:33

December 7, 2016

ሴትን አንኳስሶ የሚናገር ከራሱ ነው ክህደት የሚፈፅመው። ያ ባይሆን ደግሞ፥ አለማወቁን ነው...

ሴትን አንኳስሶ የሚናገር ከራሱ ነው ክህደት የሚፈፅመው። ያ ባይሆን ደግሞ፥ አለማወቁን ነው የሚገልጠው። ይገልጠው አለማወቅ ባይኖረው፥ አውቆ ቸል ማለቱን ያሳያል። ወይም፥ ከእውቀቶቹ ሁሉ “ሴት”ን በአግባቡ ማወቅ ጎድሎት ሳይሆን አይቀርም። ወይ ደግሞ፥ ያልተጣራ የውስጥ ችግር ይኖራል። – እንጂማ፥ “ካላበደ በቀር ዱባ ቅል አይጥልም” እንዲሉ፥ ማንም ስለፆታው ያደረገው አስተዋፅኦ በሌለበት ሁኔታ፥ ፆታው ከርሱ የተለየውን ዝም ብሎ አይፈርጅም።


 


ሴት የሚለው ቃል እንደ ቅፅል፥ ፆተኝነትን አቀንቃኝ ያልተገባ ልማዳዊ አጠቃቀም እንዳለው ቢታወቅም፥ እንደ ስም፥ የወል መጠሪያ ነው። …እንደ ወል ስም፥ ሴት: ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከመሀይም እስከ ምዑር፣ ከቤት እመቤት እስከ ድርጅት እመቤት፣ ከምንዝር እስከ አለቃ፣ ከወላድ እስከ መሀን፣ ከወታደር እስከ ጦር መሪ፣ ከአገልጋይ እስከ እመ ምኔት፣ ከፀሐፊ እስከ አንባቢ… ሌላም ከ—እስከ ተብሎ ተዘርዝሮ የማያልቅ የተለያዩ የኑሮ እርከኖች ላይ የሚገኙ፣ በተፈጥሮአዊ ባህርያቸው እንስት የሆኑ ሰዎች ተለይተው ይታወቁበታል።


 


“ሴት” ብሎ በጅምላ የሚዘልፍ፣ የሚሰድብና ደምሳሳ ድምዳሜ (hasty generalization) የሚያደርግ ፆተኛ፥ የስኬት መሰረት የሆኑ የታፈሩና የተከበሩ ሴቶችን ታሪክ አያውቅም። ወይም እያወቀ እንዳላወቀ ሆኗል። …እያወቁ እንዳላወቁ መሆን ደግሞ ካለማወቆች ሁሉ የከፋና በራስ ጥመት የሚመጣ በመሆኑ፥ ይበልጥ የማህበረሰብ እና የጋራ ግንዛቤዎች ጠንቅ ይመስለኛል።





 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on December 07, 2016 15:37

October 25, 2016

ሲደፈርስ!

ትግሉ መስመር እስኪይዝ ድረስ፥ እንኳን በኢትዮጵያ አንድነት ከሚያምኑ ኦሮሞዎች ጋር መስማማት ቀርቶ፥ የአማራ እና የኦሮሞ ዛፍነትና የስሮቻቸው ተጨባባጭነትም ይቀነቀናል። እስከዚያ፥ ተመልካች (audience) እየለዩ፥ ዓላማን ለመሸፋፈን እና ወቅታዊ ተቀባይነትን ለማግኘት፥ በየቋንቋው የተለያየ ነገር ያስተላልፋሉ። ስጋቱን ለመግለጽ የሚሞክር ቢኖር፥ በ“ትግል አታዳክም” ታፔላ ሊሸማቀቅ ይዳከራል። ትግሉ መስመሩ ተጠናክሮ ዳር ሊይዝ አጥቢያው ሲመስል ደግሞ፥ “አገር ይፍረስ! እንክትክቱ ይውጣ!” ይባላል።


 


ይገርመኛል! ፊደል መቁጠር ለዚህ ለዚህ ካልጠቀመ ለምን ሊጠቅም ነው? በተለይ በባዕድ አገር ላይ፥ “ከየት ነህ? ማን ነህ? ምን ቋንቋ ትናገራለህ? ለምን መጣህ?” ሳይባል፣ ተመቻችቶለት እንደልቡ እየኖረ እና እንደ ኅብረተሰቡ አካል ተመሳስሎ እየተማረ፣ በሞያው እያገለገለ፣ መብቱን አስከብሮ ሸጦ ለውጦ እየተዳደረ፣ ቢሻው ሀብት ንብረት እያፈራ እና ቋሚ እሴት እያጠራቀመ፥ እንዴት ለገዛ ወገኑ እልቂት መፈራረስን ይመኛል? በእንግድነት በተድላ ከሚኖርበት ቦታ እንኳን እንዴት ይህንን ትምህርት አልቀሰመም? እንዴት በመከራ ውስጥ ሆኖ ነጻነቱን ሲፈልግ፥ ባልጠገበ አንጀቱ በአምባገነን ስርዓት ወድቆ የቀረ ወገኑ ደም ላይ ይሳለቃል?


 


ይኽስ ማንን ይጠቅማል? ሰድቦ ለሰዳቢ አሳልፎ ለመስጠት ካልሆነ፥ ማንን ወደፊት ያራምዳል? እስከመቼስ በአንድነት እና በትብብር አብሮ የሚኖረው ሕዝብ፣ በሆዳም ‘አዋቂ’ ነን ባይ ፖለቲከኞች “አይ አብረህ መኖር አትችልም” ይባልለታል? ለእነሱ አገር በማፍረስ ዋጋም ቢሆን የሚገኝ የስልጣን ጥማት ማርኪያነት ለምን ይናፈቃል? ትናንት የመጡትስ ከዚህ መች ተለይተው ጀመሩት? ደግሞ፥ “ይሁን” ቢባልና ቢሳካስ በሰላም መኖር ይቻል ይመስላቸዋል? ወይስ በቃ አገሪቱን ተቃርጠው በየክልሉ ተመሳፍነው ሊያስገብሩ ነው?


 


እንዲህ ዓይነቱ ጨዋታ፥ የሴረኞችን ህልም ከማሳካት ይልቅ፥ ሙሉ አገሩ ስለአንድነቱ በጋራ እንዲቆም እንደተላለፈ ጥሪ የሚቆጠር ነው። አገራችን በጨካኝ ስርዓት እጅ ባለችበት በዚህ ሰዓት፥ ‘አገር አፍራሽ ሆነን፣ ልንበትንህ መጥተናል። እኛ መሲህ ነን’ ዓይነት ነጋሪት ብትጎስሙበትና ከያዘው ትግል ልታጓትቱት ብትጥሩ፥ አይምራችሁ! የነጭ ስልጣኔ፣ ገንዘብና የተሻለ ኑሮ ሳያጓጓቸው በባዶ እግር እና በጨበጣ ውጊያ ጣሊያንን እንኳን ገርፎ የመለሰ ሕዝብ አገር ሰዎች ነንና መቼም አይሳካላችሁም!


 


መተዋወቅ ያስፈልጋል። ስለማታውቁት፣ ወይም ድሮ አውቃችሁት ስለረሳችሁት ሕዝብ ነው የምትደሰኩሩት። “ዶሮ ብታልም ጥሬዋን” እንዲሉ፥ መከራ የፈነቀለውን እና በጋራ የቆመውን ሕዝብ “የኔ ጦር ነው…የኔ” ትባባሉበታላችሁ። ቢቆስል፥ ‘የውሻ ቁስል ያድርግልህ’ ያላላችሁትን፣ ቢሞትበት፥ የቤተሰቡን ትኩስ አስከሬን ፎቶ በየገጹ ከመቀባበል ያላላፈ፥ ጠንከር ያለ “ነፍስ ይማር” እንኳን ያላላችሁለትን፥ ደሙን ገብሮ ነጻነቱን ለመቀዳጀት ደፋ ቀና ሲል… ‘እኛ ነበርን እግዚአብሔሮችህ፣ ከኋላህ ቆመን በለው በለው ስንልህ የነበርን። አሁን ድል አገናኝቶን የባንዲራህን ጨርቅ አስቀድደን፣ ልንሰቅልልህና ልናሸጋግርህ መጥተናል’ ብትሉት አይሰማችሁም። ኢህአዴግም በብዙ ነገር ከፋፍሎ፣ በትንሽ ትንሹ ጠርንፎ፣ በሀውልትና በፕሮፖጋንዳ፣ ‘በታትኜ ያዝኩት’ ያለው ሕዝብ፥ አንድ ሆኖ እያስደነበረው ነው።


 


አሰቃቂው የኢሬቻ እልቂት ሳይቀር እንኳን፥ እንደጥሩ ትግል ማቀጣጠያ ቤንዚንነት ያስደሰታችሁና፣ እንደ ጥብስ ወሬ ያነቃቃችሁ፥ “የአገር መፍረስ ህልመኞች” እንዳላችሁ ልባችሁ የሚያውቅ ታውቁታላችሁ። ቱኒዚያ ቦአዚዝ ራሱን ቢለኩስ፥ ቤንዚን ሆኖ የነጻነት መንገድ እንደጠረገላቸው፣ ለግብጽ አብዮትም የካሊድ ሰይድ ግፈኛ አገዳደል እርሾ ሆኖ እንዳሰባሰባቸው፥ ሰው በሞተ ቁጥር ህልማችሁን የማሳካት ሴራችሁ ከግብ እንደተቃረበ በመቁጠር ብቻ… በመሰባሰብ ፈንታ፣ ‘የድል ዋዜማ ላይ ነንና ብቻችንን እንቁም’ በሚል ብልጣብልጥነት ስንቱን ለማግለል እንደጣራችሁም፣ ስንቴ በጠላት እንዳሳለቃችሁብን የምታውቁ ታውቁታላችሁ። ኦሮሞ ያልሆነ ሰው የኦሮሞ ፖለቲካ ላይ ሀሳብ ቢሰጥ፥ በ’oromophobia’ ፈርጃችሁት፣ ፍርሀትን ለመትከል የለፋችሁም ታውቁታላችሁ።


 


“እንለይህ” የምትሉት ወገን፥ በጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ እንኳን አንድ ቦታ የተከማቸ፣ ባህሉንም ያልተወራረሰ አይደለም። እንለይህ የምትሉት ወገን፥ እንጀራ ተበዳድሮ እና ሚጥሚጣ ተዋውሶ፣ ለቡና እየተጠራራ፣ ልጁን እርስ በርስ እየተቀጣጣ፣ ቤቱን ቁልፍ አልባ ትቶት “መጣሁ” ተባብሎ የኖረ ነው። ጡት ሳይቀር ተጋርቶ ያደገው ሕጻን ብዙ ነው። በከተሞች ብልጭ ድርግም ባይ መብራቶች የተጋረደ ብዙ ያልታየ ሕዝብ አለ። በአካባቢ መቀየር እንኳን የኑሮ ቀውስ የሚገጥመው ሕዝብ ነው።


 


“ጠላቶችህ ናቸው” ብላችሁ ስለወዳጆቹ ክፉ ለመንገር የምትደክሙለት ሕዝብ ያን ያህልም ክፉና ደግ የማይለይ እንዳልሆነ እንኳን አትገነዘቡም። ንቃችሁት ተነስታችሁ ነው እናስከብርህ የምትሉት። ከዚህ በላይ ‘እየታገልኩልህ ነው’ የሚሉትን አለማወቅ የለም!


 


የወገኖቻችን ደም በከንቱ ፈሶ አይቀርም!


 


ይጮሃል! ሁሌም ይጮኻል! ከጩኸቶቹ ሁሉም የጎላና የከበደ የሚሆነው፥ ‘ምሁራን’ ተሰብስበው ደሙን ሊያቃልሉበትና፣ ለጠላቶቹ መስዋዕት ሊገብሩበት እንደሆነ ያወቀ ጊዜ ሳይሆን አይቀርም።


 


የደፈረሰው ጠርቶ፣ የተከፈለው መስዋዕት እንደሚያጠባብቀንና ልቦቻችንን አክሞ በጋራ እንደሚያኖረን፣ አገሪቱንም ለሰው ልጆች ሁሉ የሚመች ስርዓት የሰፈነባት እንደሚያደርግ አልማለሁ!


 


ከዛሬ ነገ ይሻላል!


 


#Ethiopia

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on October 25, 2016 20:39

October 8, 2016

It will not be far…

The internet blackout and blockage of social networks in #Ethiopia is a blessing in disguise; and another big strategic mistake of the brutal government. It is a significant add-on to the mass protests, and tells the World once more again about the kind of government we have. As well, it has a good effect of letting the people focus on the effective and less costly interventions.


 


Our cyber activities were, somehow, keeping us aback from proper understanding of the extent that our freedom of speech is banned, and our potentials to get rid of it. Innermost, ‘being an active user of the internet’ might have created a humdrum feeling, and vapid feelings of ‘freedom fighter’ with every status update made and with every conversation held, while it hasn’t even kept us an inch closer to what is required and to our capacity.


 


If people are forced to logout facebook and other social networks, what the hell the tyrants are expecting them to do? They will login to the real world, and get organised in their communities to the fullest, so as to let brutality logout of the land for once and for all. The brutal regime is working hard to let that materialize, and organizing the people for a good cause of getting freedom.


 


Change is inevitable!, as “change will not come if we wait for some other person or some other time. We are the ones we have been waiting for. We are the change that we seek.” (Barack Obama) …and here we’re awake!, and we’ll stay united!


 


We have also learned that violence is a magic that multiplies defiant souls. When problems become devastating, solutions are promising. Now, the country has concerned and determined citizens more than ever. And speaking up for those who can’t is being a passion and it is being less confused with hard politics, and soon freedom will be a fashion for us to cherish and for our children to live in.


 


I am too positive that fighting for human rights and standing up with morale, in all fields, will be ordinary, not a bravery act for few to practice it and many to get astonished about.


 


It will not be far that they will pay the price; and amid, we will thank them for they are being on the power side of the powerless.

 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on October 08, 2016 09:32

October 6, 2016

ለቁም ነገር ስንጠራ

ማፈን መፍትሄ ኾኖ ቢያውቅ ኖሮ እንዲህ ባልደነበሩ ነበር። “ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል”ን በልባቸውም ቢሆን ለራሳቸው ባልተረቱ ነበር። ይኸው አዲስ አበባም ላይ የስልክ እና የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎቾን እንዳቋረጡ ነው።


 


ይኼ ማለት፥ ምንም እንኳን በየልሳናቶቻቸው እየቀረቡ፣ የማኅበራዊ ሚዲያዎችን እና ተጠቃሚዎቻቸውን በማውገዝ እና፣ በማንቋሸሽ ቢጠመዱም፥ የሚዲያዎቹን ሚና የሚያጣጥሉት እንዳልሆነ እየመሰከሩ ነው። የሚሸበሩት በመግባባታችን መሆኑን እየተናገሩ ነው። ቆዩ! ፍቅረኛቸው ብንሆን ኖሮማ “ብቻዬን ላገኝሽ ብጓጓ፣ ኢንተርኔት እስካቋርጥ… ስልኬን እስካዳፍን ድረስ ራድኩልሽ” ብለው ግጥም ሳይጽፉልንም አይቀሩ ነበር።


 


“ሥራ ያጣ ቄስ ቆብ ቀዶ ይሰፋል” ሲባል ዝም ብሎ ነገር ማሳመሪያ ተረት እንደኾነ አድርገው ቆጥረውት ይሆናል። የረባ ነገር አስበው አያውቁምና አልፈርድባቸውም!


 


የሕዝብን ገንዘብና የአገርን ሀብት እየበዘበዙ በሙስና ሲጨማለቁ፥ ‘ኢኮኖሚውን ምን ቀይሰን እናሳድገው? ምን የሥራ መስክ እንፍጠርለት? እንዴት እናሳትፈው፣ በገዛ አገሩ እንዲሰማው ያደረግነውን የእንግዳነት ስሜቱን በምን እንቅረፍለት?’ ብለው ተጨንቀው የማያውቁለት ስንትና ስንት ተመርቆ ቁጭ ያለ ለጋ ወጣት፣ ሥራ ፈልጎ ቢያመለክት ያሸበረቀ የባለሞያ ሲቪው እንዲታይለት ዘመድ ወይም የፖለቲካ ተሳትፎ እያስፈለገው፥ ተስፋ ይኾናል ሲባል ከኅሊናው ጋር እየተሟገተ ተስፋ ቆርጦ ቁጭ ያለ ወጣት፣ ከቤተሰብ በሚያገኘው ድጎማም ቢሆን ኢንተርኔት ላይ ቢጣድ፥ በሥራ ተጠምዷልና ስጋት ይቀንሳል።


 


ሌላም፥ ተጠቃሚውም ሰው በሚጽፋቸው ስታተስ አፕዴቶች እና በሚሰጣቸው አስተያየቶች የተነሳ “እየታገልኩ ነው” ብሎ ማሰቡና ራሱን ማጽናናቱ አይቀርም። ኢንተርኔቱ ሲቋረጥ ግን፥ በየፌስቡኩ መገናኘት የለመደ ሰው፣ መንደር የመቀየር ያኽል face to face መገናኘትን ማሰቡ አይቀርም። ይኼ ትንበያ አያሻውም። የኖርንበት ነው።


 


ቤት ውስጥ ሆነን፣ ኢንተርኔት ሲቋረጥ ከፌስቡክ ወጥተን ቤተሰቦቻችን ጨዋታ መሀል ገብተን እናውቃለን። ለጨዋታም ቢሆን ቤተሰቦቻችን ለቁም ነገር ሊያገኙን ሲፈልጉ የኢንተርኔት አፓራተሶቻችንን ደብቀውብን ያውቃሉ። ኔትዎርክ ሲቋረጥ ለሻይ ተሰብስበን ስልኮቻችንን መነካካቱን ትተን እርስበርስ ማውራት ጀምረናል። ያለንበትን የኑሮ ዓይነት እና አካባቢውን ቃኝተን “ምን እናበርክት?” ብለናል። ደጃፍ ላይ እንኳን “ችግኝ እንትከል” ተባብሎ የሚስተባበረው ከኢንተርኔት ላይ ወጥተው ሰፈር ውስጥ ሲገኙ ነው።


 


አንክድም፥ ዕውቀት ገብይተንበታልና የኢንተርኔት ሱሰኞች ኾነናል! ብድግ ብለው፣ ያላስታመሙት ሱሰኛ ሱስ ላይ በር መዝጋት ምን ዓይነት ተጽህኖ እንደሚፈጥር፥ የጭቆና እና የገዳይነት ሱሰኞች ናችሁና አይጠፋችሁም። አሁን ምን ጎድሎበትና ምን አግኝቶ ፌስቡክ ውስጥ ሲሸሸግ ሱሰኛ እንደሆነ ያውቃል። ሳይወድ በግዱም የጎደለበትን ይፈልጋል። ምስጋና ግንኙነት ያቋረጠ መስሎት፣ በአካል የመራራቅ ምሽጉን እየሰበረ ላለው አምባገነኑ መንግስት!


 


አሁን መንግስት ወጣቱን ለቁም ነገር ሳይፈልገው አልቀረም ኢንተርኔቶችን ዘግቷል። እንጂማ ሰላሙን ቢፈልግ፣ እንኳን ኢንተርኔት ሊያጠፋ፣ ዜንጦ ስልኮች (smart phones) የሌላቸውን ኹሉ ከሲም ካርድ እና ነጻ የአየር ሰዓት ጋር እያስታጠቀ በየማኅበራዊ ድረ ገጾች እንዲመሽግ ያደርገው ነበር።
 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on October 06, 2016 16:35

ዮሐንስ ሞላ's Blog

ዮሐንስ ሞላ
ዮሐንስ ሞላ isn't a Goodreads Author (yet), but they do have a blog, so here are some recent posts imported from their feed.
Follow ዮሐንስ ሞላ's blog with rss.