ሰፈሬ ልጅ ገና ሊወድቅ ሲያስብ፥
“አንተ ልጅ ዋ… ቀስ ብለህ ተጫወት…”
“ዋ ብያለሁ…”
“እሺ ኋላ እሪ ብትል ምናለች እንዳትል…”
“ትደፋና ኋላ…ዋ”
(“ውይ ተዪው አንቺ ደግሞ። ይጫወቱ እስኪ። ሸክላ ነው ልጅ ሁሉ ሲጫወት ተለይቶ ምን እንዳይሆን ነው? እሺ ከዚያስ…” የሚል ወሬ የተጠማ ድምጽ ፊቸሪን ሊገባም ይችላል።) ብዙ የማስጠንቀቂያ መዓት ይጎርፍበታል።
ልጁ ልጅ ከሆነና፥ አስጠንቃቂዋ እናቲቱ ከሆነች በዐይኗ እየተከታተለቸው ሲወላገድ ትወላገዳለች፣ ሲወድቅ ትወድቃለች። አይሞቀውም እንጂ፣ አያውቀውም እንጂ፣ አንቀልባ አልጣለችበትም እንጂ፣ እየሄደ መስሎታል እንጂ፥ በዐይኗ አቅፋው ነው የሚራመደው።
ከዚያ ተፍ ተፍ ብሎ ባፍጢሙ ይደፋላቸውና፥ አቀባብሎ እንደሚጠብቅ ሁሉ ሰፈሩ ባንድ እግሩ ይቆማል።
“ኡኡ…” ድብልቅልቁ ይወጣል።
የወደቀበትን አፈር መቃም ግዴታው ነው። አጉል አፈር አይንካኝ የሚል አፈሩን የተጠየፈ ካልገጠመው በቀር አፈሩን አቅምሶ ነው ብድግ ማለቱ የሚቀጥለው።
ከሩቅ ያዩና ያልደረሱበት “አፈሩን አቀመስሽው?” ይላሉ።
“እናትህ ትደፋ” (እንደእኔ ዓይነት ልጅ ሲሆን “የእርሶ እናት ትደፋ” ብሎ የሚሮጥበት አጋጣሚም ይኖራል።
Published on December 01, 2017 18:02