በረከታቸው ይደርብን!

10173731_1089352547747892_2394650342772072445_n




የአድዋ ድል፥ ባሰብኩት ቁጥር ህልም ህልም የሚመስለኝ ክስተት ነው። ከጦርነቱ አጃኢባትና ከድሉ ትሩፋቶች ባሻገር፥ የጀግኖቹ ደግነት ልቤን ይሰረስረዋል። ክቡር የሰውን ልጅ ሕይወት ለሀገር መስጠት የሚያስቀና ምግባር ነው። አድዋ የጦርነት ጉዳይ ብቻም አይደለም፤ ድንበር አልፎ የተዳፈረን ባለጌ የመመለስ ኃላፊነትን የመቀበል ተግባር ጭምር እንጂ። ሰው በመሆን ብቻ የሚያስቆጣ ሁኔታ ነው።


በተለይ፥ ቁስ ሳያታልላቸው፣ የመሰልጠን ተስፋ ሳያማልላቸው (ቅኝ በተገዛን ኖሮ ባደግን፥ የሚሉ ጣባ ራሶች እንዳሉ ልብ ይሏል)፣ ወላ የ“እንግዳ ተቀባይነት” ምግባራቸው እንኳን እንደ ክፉ ጥላ ሆኖ ሳያዘናጋቸው… ጠባቃ አንጀታቸውን ሸብ አድርገው፣ ሆ ብለው ጠላትን ለመመለስ የከፈሉት መስዋዕትነት የሚደንቅ ነው። ድልን መሻታቸው ፅኑ ስለነበር፥ አፍረው አልገቡም።


እርግጥ ነው፥ የተከፈለንን ነገር ለከፋዮቹ እንዳንመልስ ሁኔታዎች ላይፈቅዱልን እንደሚችሉ ይታወቃል። ነገር ግን፥ …ለቀጣዩ ክፈል (pay it forward)… የምትል፥ ፍቅራዊና ደግነታዊ አዛዥ ሀረግ አለች። ወደእኛ ሀገር ስናመጣው፥ “በረከታቸው ይደርብን” የምንለው ነገር ነው። በረከታቸው ይደርብን ስንል፥ እነርሱ ሰርተው ያለፉትን ነገር እኛም ለሌላው እናድርግ የሚል በጎ ምኞት ነው።


ታዲያ ግን፥ የአድዋ ድል በረከት አድሮብናል ወይ? ብዬ ስጠይቅ ከራሴ ጀምሮ የምታዘበው ነገር ብዙ ነው። እንደ ምሳሌ ባነሳ፥ ደጃፋችን ላይ ሰው ሲደበደብ “ወገኔ ተጠቃ” ብለን አሞን ለማስጣል እንሞክራለን? ምን ያህል የ“ድረሱልኝ” ጥሪዎች ጆሮዎቻችንን አግኝተዋል። ምን ያህል የሚፈሱ እንባዎችንና ደሞችን አይተን “ጎመን በጤና” ብለን ሸሽተናል? አፍንጫችን ስር ግፎች ሲፈፀሙ አይተን “ውሻ ምን አገባት ከሰው እርሻ”ን ተርተን ባላየ እንኖራለን? በነገሮች ላይ፥ በ“እንግዳ ተቀባይነት” ሽፋን፥ ለሌሎች ሰዎች ስናሽቋልጥ ራሳችንን ዝቅ ዝቅ አድርገናል? ስንቴስ በቁስ ተደልለናል?


“የሰው ልጅ ክቡር

ሰው መሆን ክቡር

ሰው ሞቷል – ሰው ሊያድን፣

— ሰውን ሲያከብር

በደግነት፣ በፍቅር፣ በክብር ተጠርቶ፣

በክብር ይሄዳል፥ ሰው ሊኖር — ሰው ሞቶ፤”


የአድዋ ጀግኖች በረከት ይደርብን።


ስለደግነታቸው ሁሉ እ ና መ ሰ ግ ና ለ ን!



 






 •  0 comments  •  flag
Share on Twitter
Published on February 29, 2016 04:51
No comments have been added yet.


ዮሐንስ ሞላ's Blog

ዮሐንስ ሞላ
ዮሐንስ ሞላ isn't a Goodreads Author (yet), but they do have a blog, so here are some recent posts imported from their feed.
Follow ዮሐንስ ሞላ's blog with rss.