Theodros Atlaw7 reviews25 followersFollowFollowMarch 16, 2021የሀዲስ አለማየሁ የመጀመሪያ የታተመ መጽሐፍ የሆነው “ተረት ተረት የመሠረት” በሦስት የተለያዩ ጊዜያት ይዘቱን እየቀያየረ ታትሟል፡፡ በ1948 ለመጀመሪያ ጊዜ ሲታተም አስራ አንድ ተረቶችን ይዞ ነበር፤ የ1962ኡ ሁለተኛ ህትመት የተረቶቹን ይዘት ሳይቀይር ነገር ግን አጋዥ ስዕሎች ተጨምረውበት ታተመ፤ በ1985 መጽሐፉ ለሦስተኛ ጊዜ ሲታተም፣ ስዕሎቹ ቀርተው አምስት አዳዲስ ተረቶች ታክለውበት መግቢያም ተሠርቶለት ወጥቷል፡፡ ይህ የመጨረሻው እና ተደጋግሞ የታተመው ህትመት በውስጡ አስራ ስድስት ተረቶችን የያዘ ሲሆን፣ ተረቶቹ በአብዛኛው ዋነኛ ባለታሪኮቻቸው እንሰሳት ናቸው፤ በተረቶቹ ውስጥ ሰዎች ቢገኙ እንኳን ፍዝ ሚና ኖሯቸው ነው የተመሰሉት፡፡ እንደ ሞት፣ እርጅና እና በሽታ ያሉ ረቂቅ ሀሳቦች ሥጋ ለብሰው የሚመጡበት ተረትም በመድበሉ ውስጥ ተካቷል፡፡በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የምናገኛቸው አብዛኞቹ ተረቶች ከላይ ከላይ ሲታዩ ተቀብለናቸው የምንኖራቸው ተፈጥሯዊ ሁኔታዎች፣ የሰዎች እና የእንሰሳት ግንኙነቶች፣ የእንሰሳት የእርስ በርስ ግንኙነቶች፣ የእንሰሳት ባህርያት፣ የእንሰሳት ተፈጥሮ እንዴት አሁን ያለበት ደረጃ እንደደረሰ የሚገልጡ፣ ኢሶዶሬ ኦክፔሁ "ገላጭ" የሚላቸው ዐይነት የእንሰሳት ተረቶች ናቸው፡፡ ለምሳሌ በቅሎ ለምን እንደማትወልድ፣ ጅቦች ለምን ፊትና ኋላ እንደማይሄዱ ወይም ለምን የቡዳ ምሳሌ እንደተደረጉ፣ እንሰሳት እንዴት ወደ ሳርበል እና ሥጋበልነት እንደተከፋፈሉ እና አንበሳም እንዴት "ንጉሠ አራዊት" እንደሆነ፣ እንዲሁም አይጥ እና ድመት መሐል ለምን ጠላትነት እንደተፈጠረ ይነግሩናል፡፡ ደራሲው ተረት "ተወዳጅ እንዲሆንና ደስ እያለ እንዲነበብ አፋዊ መልኩ ወይም የሞራሉ ጌጥ ደህና ሆኖ የተሰራ እንዲሆን ያስፈልጋል" እንደማለታቸው ተረቶቻቸውን በተመሠከረለት የአከያየን ክህሎታቸው አንባቢን ይዘው የሚያቆዩ አድርገው ደርሰዋቸዋል፡፡ እንደ ቃላዊው ተረት አንድ መስመር የሚከተሉ የታሪክ አወቃቀሮች፣ ያልተወሳሰቡ ታሪኮች፣ በአብዛኛው በድርጊቶቻቸው እና በንግግሮቻቸው በቀላሉ የምንተዋወቃቸው ገፀባህርያት፣ የማያደናቅፍ ቋንቋ የሀዲስ ተረቶች መለያዎች ናቸው፡፡እነዚህ ተረቶች ጽሑፋዊው የተረት ዘውግ ከቃላዊው ተረት በተዋሰው ስልት መሠረት ሁሉም ከአፋዊው አጫዋችነታቸው፣ ከጊዜ ማሳለፊያነታቸው ባሻገር ለአንባቢው (እንደየመረዳቱ) የሚሰጡት ትምህርት ወይም "ሞራል" አላቸው፡፡ ሀዲስ በተረቶቻቸው ደግነትን፣ ብልህነትን፣ ተስማምቶ መኖርን፣ ያለኝ ይበቃኛል ማለትን እና የመሳሰለውን ሲሰብኩ፤ ስግብግብነትን፣ ክፋትን፣ ከንቱ ውዳሴን፣ ሞኝነትን፣ በሌላው ላይ መፍረድን እና የመሳሰለውን ያወግዛሉ፡፡